ቅዱሳት መጻህፍት
ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ፻፬


ክፍል ፻፬

በሚያዝያ ፳፫፣ ፲፰፻፴፬ (እ.አ.አ.)፣ በከርትላንድ፣ ኦሀዮ ወይም አካባቢ ስለትብብር ድርጅት በሚመለከት ለነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ የተሰጠ ራዕይ (የክፍል ፸፰ እና ፹፪ ርዕሶችን ተመልከቱ)። ጊዜውም ምናልባት የትብብር ድርጅት አባላት በምክር ስብሰባ ቤተክርስቲያኗ ወዲያው ስለሚያስፈልጋት ለመወያየት በተሰበሰቡበት ጊዜ እንደነበር ይገመታል። ከዚህ በፊት በሚያዝያ ፲ በነበረው የድርጅቱ ስብሰባ ድርጅቱ እንዲፈርስ ተወስኖ ነበር። ይህ ራዕይ በምትኩ ይህ ድርጅት እንደገና እንዲደራጅ መመሪያ ሰጠ፤ የዚህ ንብረቶችም ለድርጅቱ አባላት በመጋቢነት ተከፋፍሎ ነበር። በጆሴፍ ስሚዝ አመራር ስር፣ “የትብብር ድርጅት” የሚባለው ሀረግ በኋላም በራዕዩ ውስጥ በ“የትብብር ስርዓት” ተተክቶ ነበር።

፩–፲፣ የትብብር ስርዓቱን የሚተላለፉት ቅዱሳን ይረገማሉ፤ ፲፩–፲፮፣ ጌታ ለቅዱሳኑን በራሱ መንገድ ያስተዳድራል፤ ፲፯–፲፰፣ የወንጌል ህግ ድሀን ስለመንከባከብ ይወስናል፤ ፲፱–፵፮፣ ለተለያዩ ወንድሞች መጋቢነቶች እና በረከቶች ተመድበዋል፤ ፵፯–፶፫፣ በከርትላንድ ውስጥ ያለው የትብብር ስርዓት እና በፅዮን ያለው ስርዓት ተለያይተው ይስሩ፤ ፶፬–፷፮፣ የጌታ ቅዱስ ሀብት ቅዱሳን መጻህፍትን ለማተም የተቋቋመ ነው፤ ፷፯–፸፯፣ የትብብር ስርዓትአጠቃላይ ሀብት በጋራ ስምምነት መሰረት ይስራ፤ ፸፰–፹፮፣ በትብብር ስርዓት ውስጥ ያሉት እዳዎቻቸውን ሁሉ ይክፈሉ፣ እና ጌታ ከገንዘብ እጦት ያድናቸዋል።

ባልንጀሮቼ እውነት እላችኋለሁ፣ የትብብር ስርዓት እና ለቤተክርስቲያኔ ጥቅምና እስከምመጣም ድረስ ለሰዎች ደህንነት እንዲሁም ዘለአለማዊ ስርዓትም ይሆን ዘንድ፣ እንዲደራጅ እና እንዲመሰረት ያዘዝኩት ንብረቶችን ስለሚመለከት ስርዓት ምክርና ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ—

ያዘዝኳቸው ታማኝ ቢሆኑ በሚበዙ በረከቶች እንዲሁም በማይለወጥ እና በማይቀየር ቃል ኪዳን ይባረካሉ፤

ታማኝ እስካልሆኑ ድረስ ግን ለመረገም ይቀርባሉ።

ስለዚህ፣ አንዳንድ አገልጋዮቼ ትእዛዜን እስካልጠበቁ ድረስ፣ በመጎምጀት እና በሀሰት ቃላት ቃል ኪዳንን ከሰበሩ ግን፣ በከፍተኛ እና አሳዛኝ እርግማን እረግማቸዋለሁ።

እኔ ጌታ በልቤ አውጄዋለሁና፣ ማንም ሰው በስርዓቱ አባል ሆኖ እየተላለፈ ቢገኘ፣ ወይም በሌላ ቃላት፣ የተሳሰራችሁበትን ቃል ኪዳን ብትሰብሩ፣ በዚህ ህይወት የረገማል፣ እና በምፈልገውም ከእግር ስር ይረገጣል።

እኔ ጌታ በእነዚህ ነገሮች አልዘበትምና

እና ይህም ሁሉ በመካከላችሁ ያሉት ንጹሕ ትክክለኛ ካልሆኑት ጋር እንዳይኮነኑ ዘንድ ነው፤ እና በመካከላችሁ ያሉት ጥፋተኞችም እንዳያመልጡ፤ ምክንያቱም እኔ ጌታ በቀኝ እጄ በኩል ለእናንተ የክብር አክሊል ቃል ኪዳን ገብቼአለሁና።

ስለዚህ፣ እንደተላላፊ እስከተገኛችሁ ድረስ፣ ቁጣዬን በህይወታችሁ አታመልጡም።

በመተላለፍ እስከተቆረጣችሁ ድረስ፣ እስከቤዛም ቀን ድረስ የሰይጣንን መንገላታቶችን አያመልጡም።

አሁንም ከመካከላችሁ ስርዓቱን ማንም ሰው ተላላፊ ሆኖ እና ለክፋቱ ንስሀ የምይገባ ሆኖ ቢገኝ፣ ለሰይጣን መንገላታት አልፋችሁ እንድትሰጡ ዘንድ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ ሀይልን እሰጣችኋለሁ፤ እና በእናንተም ላይ ክፋትን ያደርግ ዘንድ ሀይል አይኖረውም።

፲፩ ይህም በእኔ ዘንድ ጥበብ ነው፤ ስለዚህ፣ ራሳችሁን እንድታደራጁ እና ለእያንዳንዱም ሰው መጋቢነቱን እንድትመድቡ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ፤

፲፪ እያንዳንዱም ሰው ለተመደበበት መጋቢነት መልስ ይሰጠኝ ዘንድ ይሁን።

፲፫ እኔ ጌታ እያንዳንዱ ሰው ለፍጥረቶቼ ለሰራሁት እና ላዘጋጀሁት የምድር በረከቶች በመጋቢነት ተጠያቂ ይሆንም ዘንድ ፍቃዴ ነውና።

፲፬ እኔ ጌታ የእውነት የእጄን ስራ ሰማያትን ዘረጋሁ፣ እና ምድርንም መሰረትሁ፤ እና በዚህ ያሉት ነገሮች ሁሉ የእኔ ናቸው።

፲፭ እና ቅዱሳኔን ማስተዳደር አላማዬ ነው፣ ሁሉም ነገሮች የእኔ ናቸውና።

፲፮ ነገር ግን፣ ይህም በእኔ መንገድ መደረግ አለበት፤ እና እነሆ እኔ ጌታ ቅዱሳኔን ለማስተዳደር፣ ድሀዎቹን ከፍ ከፍ ለማድረግ፣ በዚያም ሀብታሞችንም ለማውረድ ይህን መንገድ አውጃለሁ።

፲፯ ምድር ሙሉ ናት፣ እና በቂና የሚተርፍም አለና፤ አዎን፣ ሁሉንም ነገሮች አዘጋጅቻለሁ፣ እና ለሰዎች ልጆችም ለራሳቸው ወኪል ይሆን ዘንድ ሰጥቻቸዋለሁ።

፲፰ ስለዚህ፣ ማንም ሰው እኔ ከሰራሁት የበዛውን ቢወስድ፣ እና በወንጌሌ ህግ መሰረት ለድሀውና ለችግረኛው ድርሻውን ባያካፍል፣ በስቃይ ውስጥ አይኑን በገሀነም ከክፉዎች ጋር ከፍ ያደርጋል።

፲፱ አሁንም ስለስርዓቱ ንብረቶች እውነት እላችኋለሁ—

አገልጋዬ ስድኒ ሪግደን አሁን የሚኖርበት ስፍራና የቆዳ ፋብሪካ መሬት ለመጋቢነቱ፣ እና እኔ እንደ ፈቃዴ፣ እርሱን በማዝበት ጊዜ በወይን ስፍራ ሲያገለግል ይደገፍበት ዘንድ ይመደብለት።

፳፩ እና ሁሉም ነገር በከርትላንድ ምድር ውስጥ በሚኖረው በስርዓቱ ሸንጎ፣ እና በጋራ ስምምነት ወይም በስርዓቱ ድምፅ መሰረት ይደረግ።

፳፪ እና ይህን መጋቢነት እና በረከት እኔ ጌታ በአገልጋዬ ስድኒ ሪግደን ላይ ለእርሱ እና ከእርሱ በኋላ ለሚመጣው ዘሩ በረከት ይሆን ዘንድ እሰጠዋለሁ።

፳፫ እና በፊቴ ትሁት እስከሆነ ድረስ በረከቶችንም አበዛለታለሁ።

፳፬ ደግሞም፣ አገልጋዬ ጆን ጆንሰን በቀድሞው ውርሱ አማካይነት በቅያሬ ያገኘውን መሬት ለመጋቢነቱ አገልጋዬ ማርቲን ሀሪስ፣ ለእርሱ እና ከእርሱ በኋላ ላለው ዘሩ፣ ይመድብለት፤

፳፭ ታማኝ እስከሆነ ድረስ፣ በረከቶችንም ለእርሱ እና ከእርሱም በኋላ ላለው ዘሩ አበዛለታለሁ።

፳፮ እና አገልጋዬ ማርቲን ሀሪስ፣ አገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ዳግማዊ እንደመራው መሰረት፣ ገንዘቡን ቃላቴን ለማወጅ ያውለው።

፳፯ ደግሞም፣ አገልጋዬ ፍረድሪክ ጂ ዊሊያምስ አሁን የሚኖርበት አካባቢ ስፍራ ይሰጠው።

፳፰ እና አገልጋዬ ኦሊቨር ካውድሪ ለእትመት ቢሮ ይሆነው ዘንድ፣ ቁጥር አንድ የሆነ የመሬት፣ ከቤቱ አጠገብ ባለው መሬት፣ ደግሞም አባቱ በሚኖርበት ስፍራ መሬት ይሰጠው።

፳፱ እና አገልጋዮቼ ፍረድሪክ ጂ ዊሊያምስ እና ኦሊቨር ካውድሪ የእትመት ቢሮ ከሁሉም ነገሮቹ ጋር ይሰጣቸው።

እና ይህም ለእነርሱ የሚመደብላቸው መጋቢነት ይሆናል።

፴፩ እና ታማኝም እስከሆኑ ድረስ፣ እነሆ እባርካቸዋለሁ፣ እና በረከቶቻቸውንም አባዛላቸዋለሁ።

፴፪ ይህም ለእነርሱ እና ከእነርሱ በኋላ ለሚመጡ ዘሮቻቸው የመደብኩላቸው መጋቢነት መጀመሪያ ነው።

፴፫ እና፣ ታማኝ እስከሆኑ ድረስ፣ ለእነርሱ እና ከእነርሱ በኋላ ለዘሮቻቸው በረከቶችን፣ እንዲሁም ብዙ በረከቶችን፣ አበዛላቸዋለሁ።

፴፬ ደግሞም፣ አገልጋዬ ጆን ጆንሰን በውርሱ ያሉትን ቤቶቼን ለመገንባት ከተመደበው ምድር እና ለአገልጋዬ ኦሊቨር ካውድሪ ከተመደበው በስተቀር ሁሉም የሚኖርበት ቤትና ውርስ ይሰጠው።

፴፭ እና ታማኝ እስከሆነ ድረስ፣ በረከቶችን አበዛለታለሁ።

፴፮ እና በመንፈስ ድምፅ እንዲያውቅ እስከተደረገለት ድረስ፣ እና በስርዓቱ ምክር መሰረት፣ እና በስርዓቱ ድምፅ የቅዱሳኔን ከተማ ለመገንባት የተቀመጡትን መሬቶች ይሸጥም ዘንድ ፍቃዴ ነው።

፴፯ ይህም ለእርሱ እና ከእርሱ በኋላ ለዘሩ ለበረከት የመደብኩት የመጋቢነት መጀመሪያ ነው።

፴፰ እና ታማኝ እስከሆነም ድረስ የበረከቶች ብዛት አበዛለታለሁ።

፴፱ ደግሞም፣ ለአገልጋዬ ኒውል ኬ ዊትኒ አሁን የሚኖርበት ቤት እና መሬት፣ እና ግብይት ከሚገኝበት መሬት እና ህንጻ፣ እና ከግብይቱ ስፍራ በስተደቡብ ያለው መሬት፣ እና ደግሞም ፖታሽ የሚሰራበት ምድር ይመደብለት።

እና ይህን ሁሉ ለአገልጋዬ ኒውል ኬ ዊትኒ ለመጋቢነት የመደብኩት ለእርሱ እና ከእርሱ በኋላ ለዘሩ በረከት፣ በከርትላንድ ምድር ውስጥ ለስቴኬ ለመሰረትኩት ግብይት ይሆን ዘንድ ነው።

፵፩ አዎን፣ በእውነት ይህም፣ እንዲሁም የግብይይቱ ስፍራ ሁሉ፣ ለአገልጋዬ ኤን ኬ ዊትኒ፣ ለእርሱና ለወኪሉ እና ከእርሱም በኋላ ለዘሩ የመደብኩት መጋቢነት ነው።

፵፪ እና የሰጠሁት ትእዛዛቴን ለመጠበቅ ታማኝ እስከሆነ ድረስ፣ ለእነርሱ እና ከእነርሱ በኋላ ለዘሮቹ በረከቶችን፣ እንዲሁም የተትረፈረፉ በረከቶችን፣ አበዛላቸዋለሁ።

፵፫ ደግሞም፣ አገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ዳግማዊ ለሁለት መቶ ሜትር ርዝመት እና ስልሳ ሜትር ስፋት ያለው ለቤቴ መገንቢያ ይሆን ዘንድ የተቀመጠው መሬት፣ ደግሞም አባቱ አሁን በሚኖርበት ውርስ ይመደብለት።

፵፬ ይህም ለእርሱ እና ከእርሱ በኋላ ለዘሩ፣ ለእርሱ እና ለአባቱ በረከት፣ የመደብኩለት መጋቢነት መጀመሪያ ነው።

፵፭ እነሆ፣ አባቱ ይረዳበት ዘንድ ወርስን አስቀምጫለሁና፤ ስለዚህ እንደአገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ዳግማዊ ቤት አባልም ይቆጠራል።

፵፮ እና በአገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ዳግማዊ ታማኝ እስከሆነ ድረስ በቤቱ በረከቶችን፣ እንዲሁም የተትረፈረፉ በረከቶችን አበዛለታለሁ።

፵፯ አሁንም ስለፅዮን በሚመለከት ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ፣ እንደትብብር ስርዓት በፅዮን ካሉት ወንድሞቻችሁ ጋር፣ ከዚህ ጉዳይ በስተቀር፣ ከዚህ በኋላ እንዳትተሳሰሩ—

፵፰ ከተደራጃችሁ በኋላ፣ በከርትላንድ ከተማ ውስጥ የፅዮን ካስማ የትብብር ስርዓት ተብላችሁ ትጠራላችሁ። እና ወንድሞቻችሁም፣ ከተደራጁ በኋላ፣ የፅዮን ከተማ የትብብር ስርዓት ተብለው ይጠራሉ።

፵፱ እና በራሳቸውም ስሞች፣ እና በራሳቸው ስምም ይደራጁ፤ እና የራሳቸውንም ጉዳይ በራሳቸው ስም፣ እና በራሳቸው ስሞችም፣ ያድርጉ፤

እና የራሳችሁንም ስራ በስማችሁ፣ እና በስሞቻችሁም አድርጉ።

፶፩ እና ይህ እንዲደረግ የማዝዘው እነርሱ በመሰደዳቸው እና ወደፊት ለሚመጣው ደህንነታችሁ፣ እና ለእነርሱም ደህንነት ነው።

፶፪ በመተላለፍ፣ በመጎምጀት እና በሀሰት ቃል በኩል ቃል ኪዳን ስለተሰበረ—

፶፫ ስለዚህ፣ ከወንድሞቻችሁ ጋር የነበራችሁ የትብብር ስርዓት ፈርሷል፣ እና እንዳልኩት በዚህ መንገድ፣ ይህ ስርዓት፣ ሁኔታችሁ በሚፈቅደው እና በሸንጎው ቀጥተኛ ድምፅ፣ ከዚህ ሰዓት በኋላ ከእነርሱ ጋር የምትተሳሰሩት በሸንጎ በሚስማሙበት ብድር ብቻ ነው።

፶፬ ደግሞም፣ የመደብኩላችሁን መጋቢነት በተመለከተ ትእዛዝን እሰጣችኋለሁ።

፶፭ እነሆ፣ እነዚህ ንብረቶች ሁሉ የእኔ ናቸው፣ አለበለዚያም እምነታችሁ በከንቱ ነው፣ እና እናንተም ግብዞች ናችሁ፣ እና ለእኔ የገባችሁትም ቃል ኪዳን ተሰብሯል፤

፶፮ እና ንብረቶቹ የእኔ ከሆኑ፣ እናንተም የእኔ መጋቢዎች ናችሁ፤ አለበለዚያ መጋቢዎች አይደላችሁም።

፶፯ ነገር ግን፣ እውነት እላችኋለሁ፣ በቤቴ ላይ መጋቢ፣ እንዲሁም በእርግጥም መጋቢዎች ትሆኑ ትሆኑ መድቤአችኋለሁ።

፶፰ እና ለዚህ አላማ ራሳችሁን እንድታደራጁ፣ እንዲሁም የቅዱስ መጻህፍቶቼን፣ የሰጠኋችሁን፣ ከዚህ በኋላም ከጊዜ ወደ ጊዜ የምሰጣችሁን ራዕዮች፣ እና የቃላቴን ሙላት እንድታትሙ አዝዤአችኋለሁ—

፶፱ ቤተክርስቲያኔን እና መንግስቴን በምድር ላይ ለመገንባት ባለኝ አላማ፣ እና ቅርብ ለሆነው፣ ህዝቤንም አብሬ ከእነርሱ ጋር ለምኖርበት ጊዜ አዘጋጃቸውም ዘንድ ነበር።

እና ለራሳችሁም የግምጃ ቤት አዘጋጁ፣ እና በስሜም ቀድሱት።

፷፩ እና ከመካከላችሁ አንዱ የግምጃ ቤቱን እንዲጠብቅ መድቡ፣ እና ለዚህ በረከትም ይሾማል።

፷፪ እና በግምጃ ቤቱም ላይ ማህተም ይኖራል፣ እና ሁሉም ቅዱስ ነገሮች ወደ ግምጃ ቤት ይወሰዳሉ፤ እና ከመካከላችሁ ማንም ይህን፣ ወይም ማንኛውንም ክፍል፣ የራሴ ነው ብለው አይጠሩትም፣ ይህም በአንድ ስምምነት ለሁላችሁም ይሆናልና።

፷፫ ደግሞም ይህን ከዚህ ሰዓት ጀምሮ እሰጣችኋለሁ፤ እና ይህም እንዲደረግ አድርጉ፣ ሂዱ እና እንዳልኩት እነዚህን የተቀደሱ ነገሮችን ለማሳተም ለዚህም አላማ፣ ከቅዱሱ ነገሮች በስተቀር፣ የተመደበላችሁን መጋቢነት ተጠቀሙበት።

፷፬ እና የቅዱስ ነገሮች ትርፍም በግምጃ ቤት ውስጥ ይቀመጥ፣ እና ማህተሙም በዚህ ላይ ይሁን፤ እና በስርዓት ድምፅ ወይም በትእዛዝ ካልሆነ በስተቀር፣ በማንም ሰው ይህን ነገር አይጠቀምበት ወይም ከግምጃ ቤቱ አያውጡት፣ ወይም የታተመበትም አይፈታ።

፷፭ እንደዚሁም የቅዱስ ነገሮችን ትርፍ፣ ለተቀደሰ እና ቅዱስ አላማ፣ በግምጃ ቤት ትጠብቃላችሁ።

፷፮ እና ይህም የጌታ የተቀደሰ ግምጃ ቤት ይባላል፤ እና ለጌታ ቅዱስ እና የተቀደሰ ይሆን ዘንድ ማህተምም ይታተማል።

፷፯ ደግሞም፣ ሌላ ግምጃ ቤት ይዘጋጅ፣ እና የንብረት ሀላፊ የግምጃ ቤትን እንዲጠብቅ ይመደብ፣ እና በዚህም ላይ ማህተም ይደረግ፤

፷፰ እና የመደብኩላችሁን ንብረቶች፣ በቤቶች፣ ወይም በመሬቶች፣ ወይም፣ ለቅዱስ እና ለተቀደሰ አላማ ከምጠብቃቸው ከቅዱስ እና ከተቀደሱ ፅህፈቶች በስተቀር በሁሉም ነገሮች በማሻሻል በመጋቢነታችሁ የተቀበላችሁት ገንዘብ በመቶዎች፣ ወይም በሀምሳዎች፣ ወይም በሀያዎች፣ ወይም በአስሮች፣ ወይም በአምስቶች ሁሉ ወደ ግምጃ ቤቱ ገንዘቡ ወዲያው እንደተቀበላችሁ አስገቡት።

፷፱ ወይም በሌላ አባባል፣ ማንኛውም ሰው አምስት ብር ቢያገኝ ወደ ግምጃ ቤት ያስገባው፤ ወይም አስር፣ ወይም ሀያ፣ ወይም ሀምሳ፣ ወይም መቶ ቢያገኝ እንዲሁ ያድርግ፤

እና በመካከላችሁ ማንም ሰው የእኔ ነው የሚለው አይኑር፤ ይህ ወይም ማንኛውም ክፍል፣ የእርሱ ተብሎ አይጠራምና።

፸፩ እና በስርዓት ድምፅ እና በጋራ ስምምነት ካልሆነ በስተቀር፣ ማንኛውንም ክፍል አይጠቀሙበት ወይም ምንም ነገር ከግምጃ ቤቱ አይውጣ።

፸፪ እና ይህም የስርዓት ድምፅ እና የጋራ ስምምነት ይሆናል—ከመካከላችሁ ማንም ሰው ለንብረት ሀላፊው እንዲህ ቢል፥ በመጋቢነቴ እንደረዳኝ ይህ ያስፈልገኛል—

፸፫ አምስት ብር፣ ወይም አስር ብር፣ ወይም ሀይ፣ ወይም ሀምሳ፣ ወይም መቶ ቢሆነ፣ የንብረት ሀለፊው በመጋቢነቱ እንዲረዳው የሚያስፈልገውን ይሰጠዋል—

፸፬ ይህም በስርዓቱ ሸንጎ ፊት ታማኝ እንዳልሆነ እና ብልህ መጋቢ እንዳልሆነ በግልፅ እስከሚታይ ድረስ የሚያስፈልገው ይሰጠዋል።

፸፭ ነገር ግን ሁሉ አባል ከሆነ፣ እና በመጋቢነቱ ታማኝ እና ብልህ ቢሆን፣ ይህም ለንብረት ሀላፊው ምልክት ስለሚሆንለት ንብረት ሀላፊው አይከልክለው።

፸፮ ነገር ግን በመተላለፍ ምክንያት፣ የንብረት ሀላፊው ለሸንጎው እና ለስርዓቱ ድምፅ መላሽ ይሆናል።

፸፯ እና የንብረት ሀላፊው ታማኝ እና ብልህ መጋቢ ሆኖ በማይገኝበት ጉዳይ፣ ለሸንጎው እና ለስርዓቱ ድምፅ መላሽ ይሆናል፣ እና ከስፍራውም ይወጣል፣ እና በእርሱም ምትክ ሌላ ይመደባል።

፸፰ ደግሞም፣ እዳዎቻችሁን በሚመለከት እውነት እላችኋለሁ—እነሆ እዳዎቻችሁን ሁሉ እንድትከፍሉ ፍቃዴ ነው።

፸፱ እና በፊቴም ትሁት እንድትሆኑ፣ እና ይህን በረከት በቅንነት እና በየዋህነትና በእምነት ጸሎታችሁ እንድታገኙ ፍቃዴ ነው።

እና ቅን እና ትሁት እስከሆናችሁ እና የእምነት ጸሎትን እስከተጠቀማችሁበት ድረስ፣ እነሆ የማድናችሁበት መንገድ እስከምልክላችሁ ድረስ፣ የአበዳሪዎቻችሁን ሰዎች ልብ አራራለሁ።

፹፩ ስለዚህ፣ ወደ ኒው ዮርክ ወዲያው ጻፉ እና በመንፈሴ እንደተሰጣችሁም መሰረት ጻፉ፤ እና በእናንት ላይ ስቃይ ለማምጣት በአዕምሮአቸው ላይ ያለውን ይወሰድ ዘንድ የአበዳሮዎቻችሁን ልብ አራራለሁ።

፹፪ እና ትሁት እና ታማኝ ብትሆኑ እና ስሜን የምትጠሩ እስከሆናችሁ ድረስ፣ እነሆ፣ ድልን እሰጣችኋለሁ።

፹፫ ለዚህም አንዴ ከባርነታችሁ ትወጡ ዘንድ፣ የተስፋ ቃልም እሰጣችኋለሁ።

፹፬ ገንዘብ በመቶዎች፣ ወይም በሺዎች፣ እንዲሁም ራሳችሁን ከእስር ለማውጣት መበደር እስከምትችሉት ድረስ ለማግኘት እድል እስካገኛችሁ ድረስ፣ ይህ መብታችሁ ነው።

፹፭ እና በእጆቻችሁ የሰጠኋችሁን ንብረቶችም፣ ለዚህ አንድ ጊዜ ስማችሁን በጋራ ስምምነት ወይም በሌላ በመስጠት፣ ወይም መልካም በሚመስላችሁ፣ በእዳ አስይዙ።

፹፮ ይህን ልዩ መብት ለአንድ ጊዜ እሰጣችኋለሁ፤ እነሆም፣ በፊታችሁ የዘረጋሁትን ነገሮች፣ በትእዛዛቴ መሰረት ለማድረግ ብትቀጥሉ፣ ሁሉም ነገሮች የእኔ ናቸው፣ እና እናንተም የእኔ መጋቢዎች ናችሁ፣ እና መምህር ቤቱ እንዲሰበር አይፈቅድምና። እንዲህም ይሁን። አሜን።