ቅዱሳት መጻህፍት
ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ፴፩


ክፍል ፴፩

መስከረም ፲፰፻፴ (እ.አ.አ.) በነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ አማካይነት ለቶማስ ቢ ማርሽ የተሰጠ ራዕይ። ወቅቱም የቤተክርስቲያኗ ጉባዔ እንደተጠናቀቀ ወዲያውኑ ነበር (የክፍል ፴ ርዕስን ተመልከቱ)። ይህ ራዕይ ከመሰጠቱ በፊት በወሩ መጀመሪያ ላይ የተጠመቀው ቶማስ ማርሽ በቤተክርስቲያን ውስጥ በሽማግሌነት ተሹሞ ነበር።

፩–፮፣ ቶማስ ቢ ማርሽ ወንጌልን እንዲሰብክ ተጠራ እናም ስለቤተሰቡ ደህንነት ማረጋገጫ ተሰጠው፤ ፯–፲፫፣ ትዕግስተኛ እንዲሆን፣ ዘወትር እንዲጸልይ እናም አጽናኙን እንዲከተል ተመከረ።

ልጄ ቶማስ፣ በስራዬ ባለህ እምነት የተባረክህ ነህ።

እነሆ፣ በቤተሰብህ የተነሳ ብዙ መከራን አይተሀል፤ ሆኖም፣ ቤተስብህን እና አንተን አዎን፣ ህጻናት ልጆችህን እባርካቸዋለሁ፤ እናም የሚያምኑበት እና እውነትን የሚያውቁበት እንዲሁም ከአንተ ጋር በቤተክርስቲያኔ አንድ የሚሆኑበት ቀን ይመጣል።

ልብህን አንሳ እናም ተደሰት፣ የተልዕኮህ ሰዓት መጥቷልና፤ እናም አንደበትህ ይፈታል፣ እናም የታላቅ ደስታን የምስራችንም ለዚህ ትውልድ ታውጃለህ።

ለአገልጋዬ ለጆሴፍ ስሚዝ ዳግማዊ፣ የተገለጡለትን ነገሮች ታውጃለህ። ከዚህ ጊዜ ጀምሮ መስበክ፣ አዎን፣ ለነዶ ሊሆን የቀረበውን ስብል መሰብሰብ ትጀምራለህ።

ስለዚህ፣ በሙሉ ነፍስህ እጨድ፣ እናም ኃጢአትህም ተሰርዮልሀል፣ እናም ብዙ ነዶም በጀርባህ ትሸከማለህ፣ ለሰራተኛ ደመወዙ ይገባዋልና። ስለዚህ ቤተሰቦችህም በህይወት ይኖራሉ።

እነሆ፣ እውነት እልሀለሁ፣ ከእነርሱ ለጥቂት ጊዜ ብቻ ሂድ፣ እናም ቃሌን አውጅ፣ እናም ለእነርሱም ስፍራን አዘጋጅላቸዋለሁ።

አዎን፣ የስዎቹን ልብ እከፍታለሁ፣ እናም ይቀበሉሀል። እና በእጀህም ቤተክርስቲያንን እመሰርታለሁ፤

እናም ታጠነክራቸዋለህ እናም ለሚሰበሰቡበት ቀንም ታዘጋጃቸዋለህ።

በስቃይ ታጋሽ ሁን፣ ክፉ ለሚናገሩህ ክፉ አትመልስ። ቤትህን በትህትና ግዛ፣ እናም የጸናህ ሁን።

እነሆ፣ ስለማይቀበሉህም ለአለም ሳይሆን ነገር ግን ለቤተክርስቲያኗ ሀኪም ትሆናለህ።

፲፩ እኔ ወደምፈቅደው ስፍራ ሁሉ ሂድ፣ እናም የምትሄድበት እና የምትሰራው በአጽናኙ ይሰጥሀል።

፲፪ ወደፈተና እንዳትገባ እና ደመወዝህን እንዳታጣ ዘወትር ጸልይ

፲፫ እስከ ፍጻሜው ድረስ ታማኝ ሁን፣ እኔም ከአንተ ጋር ነኝ። እነዚህ ቃላት የሰውም ሆነ የሰዎች አይደሉም፣ ነገር ግን በአብ ፈቃድ የእኔ ያዳኛችሁ የኢየሱስ ክርስቶስ ናቸው። አሜን።