ቅዱሳት መጻህፍት
ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ፳፫


ክፍል ፳፫

ሚያዝያ ፲፰፻፴ (እ.አ.አ.) በማንቸስተር፣ ኒው ዮርክ በጆሴፍ ስሚዝ አማካይነት ለኦሊቨር ካውድሪ፣ ለኃይራም ስሚዝ፤ ለሳሙኤል ኤች ስሚዝ፣ ለጆሴፍ ስሚዝ ቀዳማዊ፣ እና ለጆሴፍ ናይት ቀዳማዊ፣ የተሰጠ አምስት ተከታታይ ራዕዮች። ስማቸው የተጠቀሱት አምስት ሰዎች ሀላፊነታቸውን ለማወቅ በነበራቸው ፈቃድ ምክንያት፣ ነቢዩ ጌታን ጠይቆ ለእያንዳንዱ ሰው ራዕይን ተቀበለ።

፩–፯፣ እነዚህ ቀደምት ደቀ መዛሙርት ለመስበክ፣ ለመምከር፣ እና ቤተክርስቲያኗን ለማጠንከር ተጠርተዋል።

እነሆ፣ ኦሊቨር ለአንተ ጥቂት ቃላትን እናገራለሁ። እነሆ፣ አንተ የተባረክህ ነህ፣ እናም በምንም ኩነኔ ስር አይደለህም። ነገር ግን ወደ ፈተና እንዳትገባ ትዕቢትን ተጠንቀቅ።

ጥሪህን ለቤተክርስቲያኗ እና እንዲሁም በአለም ፊት እንዲታወቅ አድርግ፣ እናም ከዚህ ጊዜ ጀምሮ እናም ለዘለአለም እውነትን ለመስበክ ልብህ ይከፈታል። አሜን

እነሆ፣ ለአንተ ለኃይራም ጥቂት ቃላትን እናገራለሁ፤ አንትም ብትሆን በምንም ኩነኔ ስር አይደለህም እናም ልብህ ተከፍቷል እናም አንደበትህ ተፈትቷል፤ እናም ጥሪህ ለመምከር እና ቤተክርስቲያኗን በቀጣይነት ለማጠንከር ነው። ስለዚህ ሀላፊነትህ ለዘለአለም ለቤተክርስቲያኗ ነው፣ ይህም የሆነው በቤተሰብህ ምክንያት ነው። አሜን።

እነሆ፣ ለአንተ ሳሙኤል ጥቂት ቃላትን እናገራለሁ፤ አንትም እንዲሁ በምንም ኩነኔ ስር አይደለህም እናም ጥሪህ ለመምከር እና ቤተክርስቲያኗን በቀጣይነት ለማጠንከር ነው፤ እናም በአለም ፊት ለመስበክ ገና አልተጠራህም። አሜን።

እነሆ፣ ለአንተ ጆሴፍ ጥቂት ቃላትን እናገራለሁ፤ አንተም በምንም ኩነኔ ስር አይደለህም እናም ጥሪህ ለመምከር እና ቤተክርስቲያኗን በቀጣይነት ለማጠንከር ነው፤ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ እናም ለዘለአለም ይህ የአንተ ሀላፊነት ነው። አሜን።

እነሆ ለአንተ ለጆሴፍ ናይት መስቀልህን እንድታነሳ፣ በዚህም ድምጽህን አውጥተህ እንዲሁም በሚስጥር እናም በአለም ፊት፣ እናም በቤተሰብህ መካከል፣ እናም በባልንጀሮችህ መካከል፣ እናም በሁሉም ስፍራዎች እንድትጸልይ በእነዚህ ቃላት እገልጽልሀለሁ።

እነሆም፣ የልፋትህን ዋጋ ትቀበል ዘንድ፣ ከእውነተኛዋ ቤተክርስቲያን ጋር አንድ መሆን እና ለመምከር ቃልህን ዘወትር መስጠት ይህ ስራህ ነው። አሜን።