ቅዱሳት መጻህፍት
፪ ኔፊ ፲፫


ምዕራፍ ፲፫

ይሁዳና ኢየሩሳሌም ባለመታዘዛቸው ይቀጣሉ—ጌታም ለህዝቡ ይማፀናል፣ እናም ሕዝቡን ይፈርዳል—የፅዮን ሴት ልጆች በዓለማዊነታቸው የተነሳ የተረገሙና የተሰቃዩ ናቸው—ኢሳይያስ ፫ን አነጻፅሩ። ከ፭፻፶፱–፭፻፵፭ ም.ዓ. ገደማ።

እነሆም፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ ከኢየሩሳሌምና ከይሁዳ፣ ምርኩዝን፣ እና ድጋፍን፣ የዳቦን ድጋፍ ሁሉ እናም የውሃንም ድጋፍ ሁሉ ይወስዳል—

ሀያሉን ሰውና፣ ተዋጊውንም፣ ፈራጁንም፣ ነቢዩንም፣ ብልሁንና፣ ሽማግሌውን ሰው ይወስዳል፤

የሀምሳ አለቃውንና፣ የተከበረውን ሰው፣ አማካሪውንም፣ እና ብልሁን ሠራተኛና፣ ጥሩ ተናጋሪውን ይወስዳል።

እናም ልዑሎቻቸው ይሆኑ ዘንድ ሕፃናትን እሰጣቸዋለሁ፣ ሕፃናቶችም እነርሱን ይገዛሉ።

እናም ሕዝቡ ይጨቆናል፣ አንዱ በሌለኛው፣ እንዲሁም አንዱ በጎረቤቱ፤ ሕፃናቱ በሽማግሌው ላይ እንዲሁም ፀያፍ አድራጊዎች በተከበረው ላይ ይኮራሉ።

አንድ ሰው በአባቱ ቤት ውስጥ ወንድሙን በያዘ ጊዜ፣ እናም እንዲህ ሲለው፥ አንተ ልብስ አለህ፣ አለቃም ሁንልን፣ እናም ይህም ጥፋት ከእጅህ በታች እንዲሆን አትፍቀድ—

በዚያ ቀን እንዲህ በማለት ይምላል—ባለመድሀኒት አልሆንም፤ ምክንያቱም በቤቴ ዳቦም ሆነ ልብስ የለምና፤ የሕዝቡም አለቃ አታድርጉኝ።

የክብሩን ዐይን ለማስቆጣት፣ ምላሳቸውና ስራቸው ጌታን ስለሚፃረሩ ኢየሩሳሌም ፈረሰች፣ እናም ይሁዳ ወደቀች

በፊታቸው የሚታየው በእነርሱ ላይ ይመሰክራል፣ እናም ኃጢአታቸው እንደሰዶም አይነት እንደሆነ ያውጃል፣ እናም ሊደብቁት አይችሉም። በራሳቸው ላይ ኃጢያትን በማምጣታቸው ለነፍሳቸው ወዮላቸው!

የስራቸውን ፍሬ ይበላሉና፤ ፃድቃንን መልካም ይሆንላችኋል በላቸው።

፲፩ ወዮላቸው ለክፉዎች፤ ይጠፋሉና፤ የስራቸውም ዋጋ በእነርሱ ላይ ይሆናል!

፲፪ እናም ሕዝቤ፣ ሕፃናት ጨቋኛቸው ናቸው፣ እንዲሁም ሴቶች ገዢዎቻቸው ናቸው። ሕዝቤ ሆይ፣ የመሩአችሁ ያስቱአችኋል፣ እንዲሁም የምትሄዱበትንም መንገዳችሁን ያጠፋሉ።

፲፫ ጌታ ለሙግት ተነስቷል፣ እናም በሕዝቡም ላይ ሊፈርድ ቆሟል።

፲፬ ጌታ ከሕዝቡ ሽማግሌዎችና ከልዑሎች ጋር ለፍርድ ይገባል፤ ምክንያቱም የወይኑን ቦታ እና በቤታችሁ የሚገኙት ድሆችን ብዝበዛ የጨረሳችሁ እናንተ ናችሁ።

፲፭ እናንት ምን ማለታችሁ ነው? ሕዝቤን ታደቁአቸዋላችሁ፣ እና የድሆችንም ፊት ትፈጫላችሁ፣ ይላል የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር።

፲፮ ከሁሉም በላይ፣ ጌታ እንዲህ አለ፥ የፅዮን ሴት ልጆች ትዕቢተኛ ስለሆኑና አንገታቸውን በማስገግ ስለሚራመዱና በሚሄዱበት ጊዜ ዐይናቸውን በማጣቀስ፣ ፈጠን ብለው በመራመድ እናም በእግራቸው እያቃጨሉ በመሄዳቸው ምክንያት—

፲፯ ስለዚህ ጌታ የፅዮንን ሴት ልጆች ራስ በቡሃነት ይመታል፣ እናም ጌታ ሀፍረተ-ስጋቸውን ይገልጣል

፲፰ በዚያ ቀን ጌታ የሚያንቃጭለውን ጌጣቸውን፣ መርበብን፣ እና ጨረቃ የሚመስለውን የአንገት ጌጣቸውን ውበት ያስወግዳል።

፲፱ ሰንሰለቱንና አምባሩን፣ እና መሸፈኛውን

ቆብና የእግር አልቦውን፣ እና የራስ ማሰሪያውንና፣ የሽቶውን ዕቃ፣ እና የጆሮ ቀለበቶቹን፤

፳፩ ቀለበት እና የአፍንጫ ጌጥ፤

፳፪ ውድ ሱፍ ልብስንም፣ ካባውንንም፣ መጎናፀፊያውንም፣ እና ፀጉር መጠቅለያውን፤

፳፫ መስታወቱንም፣ ከጥሩ በፍታ የተሰራውንም ልብስ፥ ራስ ማሰሪያውንም፥ ዓይነ ርግቡንም ያስወግዳል።

፳፬ እናም እንዲህ ይሆናል፣ በጥሩ ሽታ ፈንታ ግማት፣ እና በመታጠቅያው ፈንታ ቀዳዳ፤ ጠጉርንም በመነቀስ ፈንታ መላጣነት፤ በተብለጨለጨው ልብስ ፈንታ ማቅ፤ በውበትም ፈንታ ጠባሳ ይሆናል።

፳፭ ወንዶችሽ በሰይፍ ጀግኖችሽም በውጊያ ይወድቃሉ።

፳፮ እናም በሮችዋ ያዝናሉ ያለቅሱማል፤ እናም ተስፋ በመቁረጥ በመሬት ላይ ብቻዋን ትቀመጣለች።