“አቢሽ፣” የመፅሐፈ ሞርሞን ታሪኮች [2023 (እ.አ.አ)]
አቢሽ
ህዝቦቿ በኢየሱስ እንዲያምኑ እየረዳች
አቢሽ ላማናዊት ለነበረች ንግስት ትሰራ ነበር። አቢሽ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ከአባቷ ራእይ ተማረች። ለብዙ አመታት በኢየሱስ ታምን እና እርሱን ለመከተል ትፈልግ ነበር። ነገር ግን ለሌሎች ላማናውያን ገና አልነገረቻቸውም ነበር።
አንድ ቀን፣ ላማናውያንን ስለ ኢየሱስ እና ስለ እግዚአብሔር ለማስተማር አሞን የሚባል ኔፋዊ ወደ መንግስቱ መጣ። ንግስቲቱ እና ንጉሱ አሞን ያስተማረውን አመኑ። ንግስቲቱ እና ንጉሱ ኢየሱስ ወደ ምድር እንደሚመጣ እና በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ ስርየትን እንዲያገኙ እንደሚያደርግ አወቁ።
አልማ 17፥12–13፤ 18፥33–36፣ 39–40፤ 19፥9፣ 13
ንግስቲቱ እና ንጉሱ መንፈስ ቅዱስ ተሰምቷቸው በጣም ደስ ስላላቸው በመሬት ላይ ወደቁ። አሞን እና አገልጋዮቹም ወደቁ። ቆማ የነበረችው አቢሽ ብቻ ነበረች።
አቢሽ ስለዚህ ተአምር ለሰዎች መናገር ፈለገች። ሰዎች የሆነውን ነገር ሲያዩ በእግዚአብሔር ኃይል እንደሚያምኑ ተስፋ አደረገች። ስለዚህ አቢሽ ከአንዱ ቤት ወደ ሌላው ሮጠች። እግዚአብሔር በንግሥቲቱና በንጉሡ ላይ ያደረገውን ሄደው እንዲያዩ ለህዝቡ ነገረቻቸው።
ብዙ ሰዎች ወደ ንግሥቲቱ እና ንጉሱ ቤት መጡ። ንግስቲቱ፣ ንጉሱ እና አገልጋዮቻቸው ሁሉ የሞቱ ይመስሉ ስለነበር ተገረሙ።
ሰዎቹ ግራ ገብቷቸው ነበር። በንግሥቲቱ እና በንጉሱ ላይ ስለሆነው ነገር ተከራከሩ።
አቢሽ ስትመለስ ሰዎቹ ሲከራከሩ ተመለከተች። እነሱ የእግዚአብሔርን ኃይል ስላላዩ አዘነች። ከዚያም ንግስቲቱን በእጇ ይዛ አነሳቻት፣ ንግስቲቱም ቆማ ኢየሱስን አመሰገነች።
ንግስቲቱ የባሏን እጅ ያዘች እሱም ቆመ። ንጉሡም ለህዝቡ ስለ ኢየሱስ ተናገረ። ከዚያም አሞን እና ሌሎች አገልጋዮችም ተነሱ። ሁሉም ኢየሱስ እንደቀየራቸው ለሕዝቡ ነገሩ። አሁን መልካም ነገር ብቻ ለመስራት ፈለጉ። ብዙ ሰዎችም አመኑዋቸው።
አቢሽ ተስፋ እንዳደረገችው ሰዎች የእግዚአብሔርን ኃይል ተመለከቱ። ብዙ ሰዎች በኢየሱስ አመኑ እንዲሁም ተጠመቁ። የእግዚአብሔር መንፈስ ከእነሱ ጋር ነበረ። በምድራቸውም ቤተክርስቲያንን አቋቋሙ። ኢየሱስ ንስሐ የሚገባን እና በእርሱ የሚያምንን ሁሉ እንደሚረዳ ተመለከቱ።