አጠቃላይ ጉባኤ
እዚህ ፍቅር ይወራል
የጥቅምት 2023 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


እዚህ ፍቅር ይወራል

እዚህ እያንዳንዱም በልባችን እና በቤታችን፣ እና በወንጌል ጥሪዎች፣ ተግባራት፣ አገልግሎት እና በበጎ አድራጎት ፍቅሩን ለመናገር እና ለመስማት እንማር።

የመጀመሪያ ክፍል ልጆቻችን ”እዚህ ፍቅር ይወራል”1 የሚለውን መዝሙር ይዘምራሉ።

አንድ ጊዜ ለእህት ጎንግ ትንሽ በአንገት ላይ የሚጠለቅ የፎቶ መያዣ ሰጠኋት። ነጥብ-ነጥብ፣ ነጥብ-ነጥብ፣ ነጥብ-ነጥብ-ሰረዝ እንዲጻፍበት አድርጌ ነበር። የሞርስ የሚስጥራዊ ጽሁፍን የሚያውቁ I፣ I፣ U የሚሉትን ፊደሎች ይገነዘባሉ። ሆኖም ግን ሁለተኛ ኮድን ጨመርኩኝ። በማንደሪን ቻይንኛ “ai” ማለት “ፍቅር” ማለት ነው። ስለዚህ፣ በድርብ የሚስጥራዊ መልእክቱ “እኔ አንቺን እወድሻለሁ” ማለት ነበር። ፍቅረኛዬ ሱዛን፣ “I, ai (爱), U.” ( “እኔ አንቺን እወድሻለሁ”)።

ፍቅርን በብዙ ቋንቋዎች እንናገራለን። የሰው ልጅ 7,168 በሥራ ያሉ ቋንቋዎችን እንደሚናገር ተነግሮኛል።2 በቤተክርስቲያን ውስጥም 575 በሰነድ ያሉ የመጀመሪያ ቋንቋዎችን እና በተጨማሪም ያነጋገር ዘይቤ ያላቸውንም ጨምሮ እናወራለን፡፡ እንዲሁም ሃሳብን፣ የቃላት አገላለጽ እና ስሜትን በኪነጥበብ፣ በሙዚቃ፣ በዳንስ፣ በአስተሳሰብ ምልክቶች፣ በውጫዊ እና በውስጣዊ የግል አገላለፅ እና በመሳሰሉት እንግባባለን።3

ዛሬ፣ ስለ ሦስት የወንጌል የፍቅር ቋንቋዎች እንነጋገር፦ የሞቀ ስሜትና የአክብሮት ቋንቋ፣ የአገልግሎትና የመስዋዕት ቋንቋ እና የቃል ኪዳን ወገንነት ቋንቋ።

በመጀመሪያ፣ የሞቀ ስሜት እና የአክብሮት የወንጌል ቋንቋ።

በሞቀ ስሜት እና በአክብሮት፣ እህት ጎንግ ልጆችን እና ወጣቶችን እንዲህ ትጠይቃቸዋለች፣ “ወላጆቻችሁ እና ቤተሰቦቻችሁ እንደሚወዷችሁ እንዴት ታውቃላችሁ?”

በጓቲማላ ልጆች “ወላጆቼ ቤተሰባችንን ለመመገብ ጠንክረው ይሠራሉ” ይላሉ። በሰሜን አሜሪካ ያሉ ልጆች “ማታ ማታ ወላጆቼ ታሪኮችን ያነቡ እና አልጋ ላይ በብርድልብስ ይሸጉጡኛል” ይላሉ። በተቀደሰችው ሀገር ውስጥ ልጆች “ወላጆቼ ከአደጋ ይጠብቁኛል” ይላሉ። በምዕራብ አፍሪካ፣ በጋና፣ ልጆች “ወላጆቼ በልጆችና በወጣቶች ግቦቼ ይረዱኛል” ይላሉ።

አንድ ልጅ፣ “ቀኑን ሙሉ ከሰራች በኋላ በጣም ደክሟት ቢሆንም እናቴ ከእኔ ጋር ለመጫወት ወደ ውጭ ትመጣለች” ብላለች። የእለት እለት መስዋዕትነቷ ዋጋ እንዳለው ስትሰማ እናቷ አለቀሰች። አንዲት ወጣት “እኔና እናቴ አንዳንድ ጊዜ ባንስማማም እናቴን አምናለሁ” ብላለች። የእርስዋ እናትም አለቀሰች።

አንዳንድ ጊዜ ወዲያው የሚነገር ፍቅር ወዲያው እንደሚሰማ እና እንደሚወደስ መገንዘብ አለብን።

በሞቀ ስሜት እና በአክብሮት፣ የእኛ ቅዱስ ቁርባን እና ሌሎች ስብሰባዎች በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያተኩራሉ። ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የኃጢያት ክፍያ በረቂቅ ስላለው ብቻ ሳይሆን፣ ግላዊ እና እውነተኛ ስለሆነው ስርየት በአክብሮት እንናገራለን። የኢየሱስ ክርስቶስን የተመለሰች ቤተክርስቲያን በትክክለኛ ስሟ፣ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን፣ በማለት እንጠራታለን። የሰማይ አባትን በምንጠራበት ጊዜ እና እርስ በርስ ስንነጋገር ሞቅ ያለ አክብሮት በተሞላበት የጸሎት ቋንቋ እንጠቀማለን። በቤተመቅደስ ቃል ኪዳኖች እምብርት ውስጥ ኢየሱስ ክርስቶስን ስንገነዘብ፣ ወደ “ቤተ መቅደስ መሄድ” የሚለውን ሃረግ አጠቃቀም በመቀነስ በበለጠ ደግሞ “በጌታ ቤት ውስጥ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት” የሚለውን እንጠቅሳለን። እያንዳንዱ ቃል ኪዳን በሹክሹክታ፣ ”እዚህ ፍቅር ይወራል” በማለት ይናገራል።

አዳዲስ አባላት የቤተክርስቲያን ቃላት ብዙውን ጊዜ መፍቻ ያስፈልጋቸዋል ይላሉ። “የካስማ ቤት” ጥሩ የበሬ ሥጋ እራት ያለበት ሊሆን እንደሚችል፣ “የአጥቢያ ሕንፃ” ሆስፒታልን ሊያመለክት እንደሚችል፣ “የፕሮግራም መክፈቻ ዝግጅቶች” ደግሞ በቤተክርስቲያኗ የመኪና ማቆሚያ ስፍራ ጭንቅላትን፣ ትከሻን፣ ጉልበቶችን እና የእግር ጣቶችን እንድንነካ እንደሚጋብዘን በማሰብ እንስቃለን። ሆኖም ግን፣ እባካችሁ፣ አዲስ የፍቅር ቋንቋዎችን አብረን ስንማር ተግባቢ እና ደግ እንሁን። ለቤተ ክርስቲያኗ አዲስ የሆነች፣ የተቀየረች ቀሚሷ በጣም አጭር እንደሆነ ተነገራት። እሷም ከመናደድ ይልቅ “ልቤ ተለውጧል፣ እባካችሁ ቀሚሶቼም እስከሚለወጡ ድረስ ታገሱ” ብላ መለሰች።4

የምንጠቀማቸው ቃላቶች ይበልጥ እንድንቀራረብ ወይም ከሌሎች ክርስቲያኖች እና ጓደኞች ሊያርቁን ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ የምንናገረው ስለ ሚሲዮናዊ ስራ፣ የቤተመቅደስ ስራ፣ የሰብአዊነት እና የበጎ አድራጎት ስራ ሌሎች በራሳችን የምንሰራ መስሎን እንዲያስቡ በሚያደርግ መንገድ ነው። ለእግዚአብሔር ስራ እና ክብር እና ለኢየሱስ ክርስቶስ መልካም ስራ፣ ምህረት እና ጸጋ እና የኃጢያት ክፍያ መስዋዕቱ ሁል ጊዜ በሞቀ ስሜት እና በአክብሮት ምስጋና እንናገር።5

ሁለተኛ፣ የአገልግሎትና የመስዋዕትነት የወንጌል ቋንቋ።

በየሳምንቱ እንደገና በቤተክርስቲያን የሰንበት ቀንን ለማክበር እንደ ለመደሰት ስንሰበሰብ፣ የቅዱስ ቁርባን ቃል ኪዳናችንን ለኢየሱስ ክርስቶስ እና አንዳችን ለሌላው በቤተክርስቲያናችን ጥሪዎች፣ በጓደኝነት፣ ማህበራዊነት እና አገልግሎት መግለጽ እንችላለን።

በየአካባቢው የቤተክርስትያን መሪዎችን ስጠይቃቸው፣ ከሁለቱም ወገን ወንድሞች እና እህቶች፣ “አንዳንድ አባሎቻችን የቤተክርስቲያን ጥሪዎችን አይቀበሉም” ይላሉ። በእርሱ በቤተክርስቲያን ውስጥ ጌታን እና እርስ በርስ ለማገልገል የሚደረጉ ጥሪዎች በርህራሄ፣ በአቅም እና በትህትና ለማደግ እድል ይሰጣሉ። ለጥሪ ስንቀባ ሌሎችን እና እራሳችንን ለማንሳት እና ለማጠናከር የጌታን መነሳሳት ልንቀበል እንችላለን። እርግጥ ነው፣ የሕይወታችን ተለዋዋጭ ሁኔታዎች እና ወቅቶች የማገልገል አቅማችን ላይ ተፅእኖ ሊያደርጉ ይችላሉ፣ ነገር ግን በፍጹም ፍላጎታችን ላይ ተፅእኖ እንዳያደርጉ ተስፋ እናደርጋለን። ከንጉሥ ቢንያም ጋር፣ “ቢኖረኝ ኖሮ እሰጥ ነበር”6 እያልን የምንችለውን ሁሉ እናቀርባለን።

የካስማ እና የአጥቢያ መሪዎች፣ የበኩላችንን እንወጣ። ወንድሞችን እና እህቶችን በጌታ ቤተክርስቲያን ውስጥ እንዲያገለግሉ ስንጠራ (እና ስናወርድ)፣ እባካችሁን በክብር እና በመንፈስ መነሳሳት እናድርግ። እያንዳንዳቸው አድናቆት እንዲሰማቸው እና ስኬታማ እንዲሆኑ እርዷቸው። እባካችሁን ከእህት መሪዎች ጋር ተመካከሩ እንዲሁም አዳምጡ። ፕሬዘደንት ጄ. ሩብን ክላርክ እንዳስተማሩት እናስታውስ፣ በጌታ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተጠራንበት እናገለግላለን፣ “ይህንንም ሃላፊነት አንድ ሰው አይሻውም ወይም እንቢ አይልም።”7

እህት ጎንግ እና እኔ በትዳር ስንጋባ፣ ሽማግሌ ዴቪድ ቢ ሃይት እንዲህ የሚል ምክር ሰጥተውናል፡ “ሁልጊዜ በቤተክርስቲያን ውስጥ ጥሪን ተቀበሉ። በተለይ በህይወት ምክንያት ጊዜ በምታጡበት ወቅት፣” እንዲህም ቀጠሉ፣ “ለምታገለግሏቸው እና ስታገለግሉም ደግሞ ለእራሳችሁ የጌታን ፍቅር ሊሰማችሁ ይገባል” ብለዋል። ለቤተክርስትያን መሪዎች ጌታን በመንፈሱ እና በቃ ኪዳኖቻችን ለማገልገል እሺ ብለን ጥሪን ስንቀበል ፍቅር እዚህ፣ እዚያ እና በሁሉም ቦታ እንደሚወራ ቃል እገባለሁ።

የጌታ ዳግም የተመለሰችው ቤተክርስቲያን የጽዮን ማህበረሰብን ማስፋፊያ ልትሆን ትችላለች። አብረን ስናመልክ፣ ስናገለግል፣ ስንደሰት እና ስለፍቅሩ ስንማር፣ እርስ በርሳችን በወንጌሉ እንጠነክራለን። በፖለቲካም ሆነ በማህበራዊ ጉዳዮች ላንስማማ እንችላለን ነገር ግን በአጥቢያ መዘምራን ውስጥ አብረን ስንዘምር ስምምነትን እናገኛለን። እርስ በርሳችን ቤት እና በጎረቤቶቻችን ውስጥ ከልባችን በመነጨ አዘውትረን ስናገለግል ግንኙነትን እናሳድጋለን እናም መገለልን እንዋጋለን።

ከካስማ ፕሬዝዳንቶች ጋር አባላትን በምንጎበኝበት ወቅት፣ በማንኛውም ሁኔታ ለአባላት ያላቸውን ጥልቅ ፍቅር ይሰማኛል። አንድ የካስማ ፕሬዝደንት፣ በካስማው አባላት መኖሪያ በመኪና አልፈን ስንሄድ፣ የምንኖረው የመዋኛ ገንዳ ባለው ቤት ውስጥም ሆነ በአፈር ቤት ውስጥ ቢሆን፣ የቤተክርስቲያን አገልግሎት ብዙ ጊዜ መስዋዕትን የሚያካትት እድል እንደሆነ ጠቁመዋል። ነገር ግን፣ በወንጌል አብረን ስናገለግል እና ስንሠዋ፣ ስህተቶችን ባነሰ መልኩ እና በበለጠ ደግሞ ሰላም እንደምናገኝ በጥበቡ ተመልክቷል። ስንፈቅድለት፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅሩን እዚህ እንድናወራ ይረዳናል።

በዚህ በጋ፣ ቤተሰባችን በሎውቦሮ እና በኦክስፎርድ፣ እንግሊዝ ውስጥ ግሩም የሆኑ የቤተክርስትያን አባላትን እና ጓደኞችን አገኘን። እነዚህ ትርጉም ያላቸው ስብሰባዎች የአጥቢያ ማሕበራዊ እና የአገልግሎት እንቅስቃሴዎች እንዴት አዲስ እና ዘላቂ የወንጌል ትስስር መፍጠር እንደሚችሉ አስታውሰውኛል። ለተወሰነ ጊዜ በብዙ በቤተክርስቲያን ቦታዎች ውስጥ፣ ጥቂት ተጨማሪ የአጥቢያ እንቅስቃሴዎች፣ በእርግጥ በወንጌል ዓላማ የታቀዱ እና የተተገበሩ፣ ለበለጠ አባልነት እና አንድነት እንደሚያቆራኙን ተሰምቶኛል።

አንድ በመንፈስ የተመራ የአጥቢያ የተግባራት ሊቀመንበር እና ኮሚቴ ግለሰቦችን እና የቅዱሳን ማህበረሰብን ይንከባከባል። የእነርሱ በሚገባ የታቀዱ ተግባራት ሁሉም ሰው አስፈላጊ እንደሆነ እንዲሰማው፣ እንዲካተት እና አስፈላጊውን ሚና እንዲጫወት ይጋብዛሉ። እንደነዚህ ያሉት ተግባራት የዕድሜ እና የማንነት ድልድይን ያገናኛሉ፣ ዘላቂ ትውስታዎችን ይፈጥራሉ፣ እና በትንሽ ወይም ያለ ምንም ወጪ ሊከናወኑ ይችላሉ። አስደሳች የወንጌል ተግባራት ጎረቤቶችን እና ጓደኞችን ይጋብዛሉ።

ማህበራዊነት እና አገልግሎት ብዙ ጊዜ አብረው ይሄዳሉ። ወጣት አዋቂዎች አንድን ሰው ለመተዋወቅ በእርግጥ ከፈለጋችሁ፣ ትርጉም ባለው የአገልግሎት ፕሮጀክት ውስጥ በመሰላል ላይ አብሮ ቆመው ቀለም መቀባት እንደሚያስፈልጋቸው ተገንዝበዋል።

ምስል
ወጣት ጎልማሶች ቀለም የመቀባት ስራ ላይ ሲሳተፉ።

በእርግጥ አንድም ግለሰብም ሆነ ቤተሰብ ፍጹም አይደሉም። እዚህ ፍቅርን ለማውራት ሁላችንም እርዳታ እንፈልጋለን። “ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል።”8 እምነት፣ አገልግሎት እና መስዋዕትነት ከራሳችን በላይ ወደ አዳኛችን እንድንቀርብ ያደርገናል። የበለጠ ሩህሩህ፣ ታማኝ እና ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ አገልግሎታችን እና መስዋዕታችን በእርሱ ውስጥ ስናደርግ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን ማለቂያ የሌለው እና ለኛ ያለውን የኃጢያት ክፍያ ርህራሄ እና ፀጋን የበለጠ ለመረዳት እንጀምራለን።

ያ ደግሞ የቃል ኪዳን ወገን ወደሚለው የወንጌል ቋንቋ ያመጣናል።

ራስ ወዳድ በሆነ ዓለም ውስጥ ነው የምንኖረው። “እራሴን እመርጣለሁ” የሚል አመለካከት አለበት። የራሳችንን ጥቅም እና እንዴት ልናሳድደው እንደምንችል በተሻለ መልኩ እንደምናውቅ የምናምን ያህል ነው።

ነገር ግን በመጨረሻ ያ እውነት አይደለም። ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን የማያረጅ እውነታ ገልጿል።

ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል ፤ ነገር ግን ለኔ ብሎ ሕይወቱን የሚያጣ ሁሉ ያድናታል።”

“ወንድ ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?”9

ኢየሱስ ክርስቶስ የተሻለ መንገድ አቅርቧል— እሱም በመለኮታዊ ቃል ኪዳን ላይ የተመሰረተ፣ ከሞት ገመዶች የጠነከረ ነው። ከእግዚአብሔር እና ከሌላው ጋር ያለን የቃል ኪዳን ወገንነት፣ በጣም የምንወደውን ግንኙነታችንን ሊፈውስና ሊቀድስ ይችላል። እንደ እውነቱ ከሆነ እርሱ እኛን በደንብ ያውቀናል እና ከምናውቀው በላይ ወይም ከራሳችን በላይ ይወደናል። እኛ በሁለመናችን ቃል ኪዳን ስንገባ፣ እኛ ከሆንነው የበለጠ ለመሆን እንችላለን። የእግዚአብሔር ኃይል እና ጥበብ በእያንዳንዱ መልካም ስጦታ፣ በራሱ ጊዜ እና መንገድ ሊባርከን ይችላል።

ጀነሬቲቭ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) በቋንቋ ትርጉም ውስጥ ትልቅ እድገት አድርጓል። ኮምፒውተር “መንፈስ ፈቃደኛ ነው ሥጋ ግን ደካማ ነው” የሚለውን ፈሊጠ ሐረግ “ወይኑ መልካም ነው ሥጋው ግን ተበላሽቷል” ወደሚለው ፈሊጠ ሐረግ የሚተረጉምበት ጊዜ አልፏል። የሚገርመው፣ ሰፊ የቋንቋ ምሳሌዎችን መደጋገም የሰዋሰው ህግን ለኮምፒውተር ከማስተማር ይልቅ ቋንቋን በብቃት ያስተምራል።

በተመሳሳይ፣ የራሳችን ቀጥተኛና፣ ተደጋጋሚ ተሞክሮዎች የወንጌል ቋንቋዎችን፣ የሞቀ ስሜት ያለውን እና አክብሮትን፣ የአገልግሎት እና የመስዋዕትነት እና የቃል ኪዳን ወገንነትን ለመማር ተመራጭ መንፈሳዊ መንገዶቻችን ሊሆኑ ይችላሉ።

ታዲያ ኢየሱስ ክርስቶስ በፍቅር የሚናገራችሁ የትና እንዴት ነው?

የሱ ፍቅሩ እዚህ ሲወራ የት እና እንዴት ትሰሙታላችሁ?

እዚህ እያንዳንዱም በልባችን እና በቤታችን፣ እና በወንጌል ጥሪዎች፣ ተግባራት፣ አገልግሎት እና በበጎ አድራጎት ፍቅሩን ለመናገር እና ለመስማት እንማር።

በእግዚአብሔር እቅድ ውስጥ፣ እያንዳንዳችን አንድ ቀን ከዚህ ህይወት ወደ ቀጣዩ ህይወት እንሸጋገራለን። ጌታን ስንገናኝ፣ በትምህርት እና በተስፋ ቃል፣ “እዚህ ፍቅሬ ይወራል” ሲል በዓይነ ህሊናዬ አስባለሁ። በተቀደሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሜን።