2010–2019 (እ.አ.አ)
መንፈሳዊ ሀብቶች
የጥቅምት 2019 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


መንፈሳዊ ሀብቶች

በጌታ እና በእርሱ የክህነት ኃይል ላይ ያላችሁን እምነት ስትለማመዱ እነዚህን ጌታ ያቀረበላችሁን መንፈሳዊ ሃብቶች የመጠቀም ችሎታችሁ ያድጋል፡፡

ለዚያ ለሚያምረው መዝሙር አመሰግናለሁ። ሁላችንም ቆመን የመሃከለኛውን መዝሙር “እግዝአብሄር ሆይ ለነብይ እናመሰግንሃለን” ስንዘምር ሁለት ሃሳቦች በሃይል ወደኔ መጡ። አንደኛው ስለመጨረሻው ዘመን ነብይ ዮሴፍ ስሚዝን ነው። ለሱ ያለኝ ፍቅር እና አድናቆት ቀን ባለፈ ቁጥር እያደገ ይመጣል። ሁለተኛው ሃሳብ የመጣው ሚስቴን፣ ሴት ልጆቼን፣ ሴት የልጅ ልጆቼን፣ እና ሴት የልጅ ልጅ ልጆቼን ሳይ ነው። እያንዳንዳችሁን እንደቤተሰቤ አካል እንድቆጥር ነው የተሰማኝ።

ከበርካታ ወራት በፊት በቤተመቅደስ ቡራኬ ክፍለ ጊዜ መጨረሻ ላይ ለባለቤቴ እንዲህ አልኳት ”እህቶች የእነርሱ የሆኑትን በቤተመቅደስ ውስጥ ያሏቸውን መንፈሳዊ ሀብቶች እንደሚገነዘቡ ተስፋ አደርጋለሁ። ” እህቶች ፣ ከሁለት ወራት በፊት እኔ እና ዊንዲ ፔንሲልቫንያ ሃርመኒን በጎበኘንበት ጊዜ ጨምሮ ራሴን ብዙውን ጊዜ ስለእናንተ እያሰብኩ አገኘዋለሁ ፡፡

ምስል
የአሮናዊ ክህነት ዳግም መመለስ

ይህ ወደዚያ ያደረግነው ሁለተኛው ጉዞአችን ነበር ፡፡ በዛ በተቀደሰ ምድር ላይ በተጓዝንበት በሁለቱም ጊዜዎች በጥልቅ ተነክተን ነበር ፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ለጆሴፍ ስሚዝ የተገለጠለት እና የአሮናዊ ክህነትን መልሶ ያቋቋመው በሐርመኒ ውስጥ ነበር።

ምስል
የመልከጼዴቅ ክህነት ዳግም መመለስ

መልከጼዴቅ ክህነትን መልሶ ለማቋቋም ሐዋሪያት ጴጥሮስ ፣ ያዕቆብ እና ዮሐንስ የታዩት እዚያው ነበር።

ነቢዩ ዮሴፍ መፅሐፈ ሞርሞንን በተረጎመበት ወቅት ኤማ ሄል ስሚዝ እንደ ባለቤቷ የመጀመሪያ ጸሐፊ ሆና ያገለገለችው በሃርመኒ ውስጥ ነበር።

በተጨማሪም ዮሴፍ ለኤማ የጌታን ፈቃድ የሚገልጥ ራዕይ የተቀበለው በሐርሞኒ ውስጥ ነበር ፡፡ ኤማ ቅዱሳት መጻህፍትን እንድታብራራ ፣ ቤተክርስቲያኗን እንድታበረታታ ፣ መንፈስ ቅዱስን እንድትቀበል እና ጊዜዋን “ብዙ በመማር” ማሳለፍ እንድትችል ጌታ መመሪያ ሰጣት። እንዲሁም ኤማ “የዚህን ዓለም ነገሮች እንድትተው እና የተሻሉ ነገሮችን እንድትፈልግ“ እናም ከእግዚአብሔር ጋር የገባችውን ቃል ኪዳኖች አጥብቃ እንድትይዝ ተመክራለች፡፡ ጌታ መመሪያውንን በእነዚህ አሳማኝ ቃላት አጠናቅቋል “ለሁሉም የሆነው ይህ የእኔ ድምጽ ነው።”1

በሃርሞኒ ውስጥ የተፈጸሙት ነገሮች ሁሉ በሕይወታችሁ ውስጥ ትልቅ አንደምታዎች አሏቸው፡፡< የክህነት ስልጣን መመለስ እና ጌታ ለኤማ የሰጠው ምክር እያንዳንዳችሁን መምራት እና መባረክ ይችላል። የክህነት ስልጣን መልሶ መቋቋም ለማንኛውም ሰው አስፈላጊ እንደሆነው ሁሉ ለእናንተም እንደሴትነታችሁ አስፈላጊ መሆኑን እንድትረዱ እፈልጋለሁ ፡፡ የመልከጼዴቅ ክህነት በመመለሱ ምክንያት ፣ ቃል ኪዳኑን የሚጠብቁ ሴቶች እና ወንዶች “የቤተክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ በረከቶች ሁሉ” ፣ ወይም ፣ ጌታ ለልጆቹ ካለውን መንፈሳዊ ሀብቶች ሁሉ መቋደስ ይችላሉ ማለት እንችላለን ፡፡2

ከእግዚአብሄር ጋር ቃል-ኪዳኖችን የገቡ እያንዳንዳቸው ሴቶች እና ወንዶች እንዲሁም እነዚያን ቃል ኪዳኖች የሚጠብቁ እና በክህነት ስርዓቶች ውስጥ በብቃት የሚሳተፉ ሁሉ የእግዚአብሔርን ኃይል በቀጥታ የመጠቀም ስልጣን አላቸው። በጌታ ቤት ወስጥ የቤትመቅደስ ቡራኬን ያገኙ በቃልኪዳናቸው አማካይነት ያንን ኃይል ለመጠቀም ከሚያስችል የእውቀት ስጦታ ጋር የእግዚአብሔር የክህንት ኃይል ይቀበላሉ ።

ሰማያት ልክ የክህነት ተሸካሚ ለሆኑት ወንዶች ክፍት እንደሚሆኑ ሁሉ የእግዚአእሔርን የቡራኬ ሀይል የተቀበሉ ሴቶች በተስጣቸው የክህነት ቃልኪዳናቸው አማካይነት ለእነሱም ክፍት፡፡ ህይወታችሁን እንደሚለውጥ ስለማምን በእያንዳንዳችሁ ልብ ላይ እውነት እንዲመዘገብ እፀልያለሁ ፡፡ እህቶች ፣ ቤተሰቦቻችሁን እና ሌሎችን የምትወዷቸውን ለመርዳት የአዳኙን ሀይል በነፃነት ወደናንተ የማምጣት መብት አላችሁ።

ለራሳችሁ እንዲህ ትሉ ይሆናል “ይህ አስደሳች ይመስላል ግን ይህንን እንዴት ማድረግ እችላለሁ?“ የአዳኙን ሀይል ወደ ህይወቴ እንዴት መሳብ እችላለሁ?”

ይህንን ሂደት በማንኛውም የአጠቃቀም መመሪያ ውስጥ ተዘርዝሮ አታገኙትም። ጌታ ምን እንድትረዱ እንደሚፈልግ ለማወቅ እና ለማድረግ ስትፈልጉ መንፈስ ቅዱስ የግል አስተማሪያችሁ ይሆናል። ይህ ሂደት ፈጣንም ቀላል አይደለም ፣ ነገርግን በመንፈሳዊ የሚያነቃቃ ነው ፡፡ የክህነት ሀይልን ለመረዳት ከመንፈስ ጋር አብሮ ከመስራት የበለጠ አስደሳች ሊሆን የሚችል ምን ነገር አለ—የእግዚያብሄርን ሃይል ለመረዳት?

ልነግራችሁ የምችለው ነገር ቢኖር የእግዚአብሔርን ሀይል በህይወታችሁ ውስጥ ለመጠቀም ጌታ ኤማ ን እና እያንዳንዳችሁን እንድታደርጉ ያዘዛቸውን ተመሳሳይ ነገሮች ማድረግን ይፈልጋል ፡፡

ስለዚህ ፣ በትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ክፍል 25 ላይ ያለውን በጸሎት መንፈስ እንድታጠኑ እና መንፈስ ቅዱስ የሚያስተምረውን እንድታገኙ እጋብዛችኋለሁ። የቡራኬውን ኃይል ስታገኙ ፣ ስትገነዘቡት እና ስትጠቀሙበት የራሳችሁ የግል መንፈሳዊ ጥረት ደስታን ያመጣላችኋል ፡፡

የዚህ ጥረት ክፍል ብዙ የዚህ ዓለም ነገሮችን ማስወገድን ይፈልግባችኋል። አንዳንድ ጊዜ አልፎ አልፎ በክርክሩ፣በተንሰራፉት ፈተናዎች እና የሃሰት ፍልስፍናዎች ምክንያት ከአለም ዞር ስለማለት እናወራለን፡፡ ነገር ግን በእውነት እንዲህ ማድረግ ሕይወታችሁን በጥንቃቄ እና በየወቅቱ እንድትመረምሩ ይፈልጋል ፡፡ ይህን በምታደርጉ ጊዜ ፣ መንፈስ ቅዱስ ከእንግዲህ ወዲህ አስፈላጊነት ስለሌለው ፣ ጊዚያችሁን እና ጉልበታችሁን ልታጠፉለት ስለማይገባው ነገር ያስገነዝባችኋል ፡፡

ትኩረታችሁን ከዓለማዊና ስሜትን ከሚስቡ ጉደዮች በምታርቁበት ጊዜ በወቅቱ አስፈላጊ ሚመስሏችሁ አንዳንድ ነገሮች የቅድሚያ አስፈላጊነታቸውን ያጣሉ፡፡ ምንም ጉዳት የማያስከትሉ ቢመስሉም እንኳን የተወሰኑ ነገሮችን አይሆንም ማለት ያስፈልጋችኋል ፡፡ ሕይወታችሁን ለጌታ መለየት ስትጀምሩ እና ይህንን የህይወት ሙሉ ሂደት ስትቀጥሉ፣ በአመለካከታችሁ ፣ በስሜታችሁ እና በመንፈሳዊ ጥንካሬያችሁ ላይ የሚከሰቱት ለውጦች ያስደንቋችኋል።

አሁን ደግም ጥቂት የማስጠንቀቂያ ቃል፡፡ የእግዚያብሄርን ሃይል ለመጠቀም ያላችሁን ችሎታ ዝቅ ዝቅ የሚያደርጉ አሉ፡፡ ራሳችሁን እንድትጠራጠሩ እና እንደ ጻድቅ ሴት ያለችሁን መንፈሳዊ ሃይል እንድታሳንሱ የሚፈልጉ አሉ፡፡

በእርግጠኝነት ጠላት በጥምቀት ጊዜ የገባችሁትን ቃል ኪዳን ምንነት ወይም በቤተመቅደስ —በእግዚያብሄር ቤት የተቀበላችሁትን ወይም የምትቀበሉትን ጥልቅ የእውቀት እና የኃይል ስጦታ እንድትገነዘቡት አይፈልግም። እናም በእርግጠኝነት በቤተመቅደስ ውስጥ በተገቢነት በምታገለግሉ እና በምታመልኩበት ጊዜ በእግዚአብሔር ኃይል እና በመላእክት“አመራር” ታጥቃችሁ የምትሄዱ እንደሆነ እንድታውቁ ሰይጣን አይፈልግም ፡፡3

የተባረካችሁትን እና ልትባረኩ የምትሉትን መንፈሳዊ ስጦታዎች እንዳትገነዘቡ ሰይጣን እና ጭፍራዎቹ ያለማቋረጥ የመንገድ መሰናክሎችን ያስቀምጣሉ። እንደ አለመታደል ሆኖ አንዳንድ የመንገድ መሰናክሎች የሌሎች መጥፎ የስነምግባር ውጤት ሊሆኑ ይችላሉ። ገለል ተደርጋችኋል ወይም በክህነት መሪ እምነት አልተጣለባችሁም ነበር ወይም በባል ፣ በአባት ወይም ጓደኛ ሊሆን በሚገባው ሰው ተጎድታችኋል ወይም ተከድታችኋል ብዬ ማሰቡ በጣም ያሳዝነኛል። ከናንተ ማንኛውም ገለል የመደረግ ፣ ክብር የመነፈግ ወይም የተዛባ ፍርድ የተሰጠው ሆኖ የሚሰማው ከሆነ ጥልቅ ሀዘን ይሰማኛል። እንደዚህ ዓይነት ጥፋቶች በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ቦታ የላቸውም ፡፡

በተቃራኒው ደግሞ፣ በካስማ እና በአጥቢያ ምክር ቤት ውስጥ የሴቶችን ተሳትፎ በጉጉት ስለሚሹ የክህነት መሪዎች ሳውቅ ደስ ይለኛል ፡፡ በጣም አስፈላጊ የሆነው የክህነት ሀላፊነቱ ሚስቱን መንከባከብ መሆኑን በተግባር በሚያሳይ በእያንዳንዱ ባል በጥልቅ ተነሳሽ እሆናለሁ።4 ሚስቱ ራዕይን ለመቀበል እና እኩል አጋር በመሆን ለትዳራቸው አስተዋፅ ለማድረግ ያላትን ችሎታ በጥልቅ ለሚያከብር ሰው አድናቆት አለኝ።

አንድ ሰው ጻድቅ፣ፈላጊ፣ቡራኬ የተቀበለች የኋለኛው ቀን ቅዱስ ሴትን ታላቅነት እና ሓይል ሲረዳ ወደ ክፍሉ ስትገባ በክብር ተነስ ቁም የሚል ስሜት ቢሰማው የሚያስገርም ነው?

ከጊዜ ጅማሮ አንስቶ ሴቶች በልዩ የሞራል አቅጣጫ መጠቆሚያ መሳሪያ ተባርከዋል—ክፉውን እና ደጉን የመለየት ችሎታ፡፡ ቃል ኪዳኖችን በሚገቡ እና በሚጠብቁት ላይ ይህ ስጦታ የጎላ ይሆናል። እንዲሁም ሆነ ብለው የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ወደጎን በሚያደርጉት ላይ ደግሞ እየቀነሰ ይሄዳል።

ትክክልና ስህተት የሆነውን ለመለየት እንዲችሉ አምላክ ከእነርሱ ከሚጠይቀው መሥፈርት ወንዶች በማንኛውም መንገድ ነጻ እንዳልሆኑ ለማከል እቸኩላለሁ ፡፡ ውድ እህቶቼ እውነታን ከስህተት የመለየት ችሎታችሁ ፣ የህብረተሰቡ የስነ ምግባር ጠባቂ የመሆን ችሎታችሁ በእነዚህ የመጨረሻ ቀናት በጣም አስፈላጊ ናቸው ፡፡ እናም ሰዎች እንዲሁ እንዲያደርጉ እንድታስተምሩ በእናንተ ላይ ተመክተናል ፡፡ እዚህ ላይ አንድ ነገር ግልጽ ላድርግ : ዓለም የሴቶችን የሥነ ምግባር ንጽህና ካጣች በጭራሽ አታገግምም ፡፡

እኛ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን ከአለም አይደለንም፤ እኛ የቃል ኪዳን እስራኤል ነን ፡፡ እኛ ለጌታ ዳግም ምፅዓት አንድ ሕዝብ እንድንዘጋጅ ተጠርተናል ፡፡

አሁን ከሴቶች እና ከክህነት ጋር የተያያዙ በርካታ ተጨማሪ ነጥቦችን ላብራራ እችላለሁን። በማንኛውም ጥሪ ለማገልገል የክህነት ቁልፎችን በያዘ ሰው ስትለዩ—ለምሳሌ በእናንተ ኤጲስ ቆጶስ ወይም የካስማ ፕሬዚዳንት —በእዚያ ጥሪ ውስጥ እንዲሰሩ የክህነት ስልጣን ተሰጥቷችኋል።

በተመሳሳይም በተቀደሰው ቤተመቅደስ ውስጥ በምትካፈሉበት ጊዜ ሁሉ የክህነት ስርዓቶችን ለመፈፀም እና ለማከናወን ስልጣን ተሰጥቷችኋል፡፡ የቤተመቅደስ ቡራኬያችሁ ይህንን እንድታደርጉ ያዘጋጃችኋል።

የቤተመቅደስ ቡራኬ የተቀብላችሁ ሆናችሁ ነገር ግን በዚህ ሰአት የትዳር አጋራችሁ የክህነት ስልጣን ተሸካሚ ካልሆነ እናም አንድ ሰው “ይቅርታ የክህነት ስልጣን ተሸካሚ በቤታችሁ የለም“ ቢላችሁ፣ እባካችሁ ያ አረፍተነገር ትክክል እንዳልሆነ ተገንዘቡ፡፡ የክህነት ስልጣን ተሸካሚ በቤታችሁ ላይኖር ይችላል ነገር ግን የክህነት ሃይል የሚያስገኘውን ቅዱስ ቃልኪዳን በግዚአብሔር ቤተመቅደስ ተቀብላችኋል፡፡ ከእነዚያ ቃል ኪዳኖች የእርሱ የክህነት ኃይል ቡራኬ በእናተ ላይ ይፈሳል ። እናም አስታውሱ የትዳር አጋራችሁ ቢሞት በቤታችሁ ላይ ሃላፊ ናችሁ፡፡

እንደ ጻድቅ የቤተመቅደስ ቡራኬን የተቀበላችሁ የኋለኛው ቀን ቅዱስ ሴት በሃይል እና ከእግዚያብሄር በተገኘ ስልጣን ትናገራላችሁ፡፡ በማበረታቻም ይሁን በውይይት የክርስቶስን ትምህርት የምታስተምሩበትን ድምጻችሁን እንፈልጋለን ፡፡ በቤተሰብ፣በአጥቢየ እና በካስማ ምክር ቤቶች የምታደርጉትን አስተዋጽኦ እንፈልጋለን፡፡ የእናንተ ተሳትፎ አስፈላጊ ነው እናም በፍጹም ጌጥ አይደለም!

ውድ እህቶቼ ሌሎችን በምታገለግሉበት ጊዜ ኃይላችሁ ይጨምራል። ጸሎቶቻችሁ፣ጾማችሁ፣ቅዱሳት ጽሁፎችን በማንበብ የምታሳልፉት ጊዜ እና የቤተመቅደስ ውስጥ እና የቤተሰብ ታሪክ ስራ አገልግሎታችሁ ሰማያትን ይከፍቱላችኋል፡፡

ስለ ክህነት ሀይል ልታገኟቸው የምትችሏቸውን እውነቶች ሁሉ በጸሎት መንፈስ እንድታጠኑ እማጸናችኋለሁ ፡፡ በትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ክፍል 84 እና 107 ልትጀምሩ ትችላላችሁ፡፡ እነዚያ ክፍሎች ወደሌሎች ምንባቦች ይመሯችኋል፡፡ ቅዱሳት ጽሁፎች እና የዘመናችን ነቢያት፣ገላጮች እና ራእይ ተቀባዮች ትምህርቶች በእነዚህ እውነቶች የተሞሉ ናቸው፡፡ ግንዛቤያችሁ ሲጨምር እንዲሁም በጌታ እና በእርሱ የክህነት ስልጣን ላይ ያላችሁን እምነት ስትለማመዱ ያቀረበላችሁን መንፈሳዊ ሃብቶች የመጠቀም ችሎታችሁ ያድጋል፡፡ ይህን ስታደርጉ አንድነት ያላቸውን፣ በጌታ ቤተመቅደስ ውስጥ የታተሙና እና በሰማይ አባታችን እና በኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር የተሞሉ ዘላለማዊ ቤተሰቦችን በተሻለ ለመፍጠር መርዳት ትችላላችሁ።

አንዳችን ለሌላው ለማገልገል ፣ ወንጌልን ለማወጅ ፣ ቅዱሳንን ፍጹማን ለማድረግ እና ለሙታን የቤተመቅደስ ስርአቶችን ለማከናወን የምናደርጋቸው ጥረቶች ሁሉ በቤተመቅደስ ይገናኛሉ ፡፡ አሁን በአለም ዙሪያ 166 ቤተመቅደሶች አሉን ሌሎችም እየመጡ ነው፡፡

እንደምታውቁት የሶልተ ሌክ ሲቲ ቤተመቅደስ ቴምፕል ስኩዌር እና ከቤተክርስቲያኗ ህንጻ ቢሮ ጋር ተያይዞ የሚገኘው ፕላዛ በአመቱ መጨረሻ ላይ በሚሰራ ፕሮጀክት ይታደሳል፡፡ ይህ የተቀደሰ ቤተ መቅደስ በዚህ በእኛ ትውልድ ላይ ተጽዕኖ እንዳሳደረ ሁሉ የወደፊቱንም ትውልድ ለማነሳሳት የተጠበቀ እና የተዘጋጀ መሆን አለበት።

ቤተክርስቲያኗ እያደገች ስትሄድ ብዙ ቤተሰቦች ከበረከቶች ሁሉ የላቀውን የዘላለም ህይወት በረከት ያገኙ ዘንድ ብዙ ቤተክርስቲያኖች ይገነባሉ፡፡5 ቤተመቅደስን በጣም የተቀደሰ መዋቅር አድርገን እንመለከታለን። አዲስ ቤተመቅደስ የመገንባት እቅድ በማስታወቂያ በሚነገርበት ጊዜ ሁሉ የታሪካችን አስፈላጊ አካል ይሆናል። በዛሬው ምሽት እዚህ እንደተነጋገርነው እናንተ እህቶች ለቤተመቅደስ ስራ አስፈላጊዎች ናችሁ፤ እንዲሁም ቤተመቅደስ እጅግ ታላላቆቹን መንፈሳዊ ሃብቶች የምትቀበሉባቸው ቦታዎች ናቸው።

እባካችሁን አሁን ስምንት አዲስ ቤተመቅደሶችን የመገንባት እቅዶችን እናገራለሁ በጥንቃቅቄ እና በማክበር አዳምጡ። የማስተዋውቀው ቤተመቅድሰ ቦታ ለእናንተ ልዩ ከሆነ፤ ምክሬ በቀላሉ እራሳችሁን በመጎንበስ ፀጥ ባለ ፀሎት ከልባችሁ እንድታመሰግኑ ነው፡፡ በሚከተሉት ቦታዎች ቤተመቅደሶችን የመገንባት እቅድ ስናውጅ በደስታ ነው፤ ፍሪ ታውን ሴራሊዮን፣ ኦረም ዩታህ፣ ፖርት ሞርስቢይ ፓፑዋ ኒው ጊኒ፣ በንቶኒል አርካንሳስ፣ ባኮሎድ ፊሊፒንስ፣ ማካለን ቴክሳስ፣ ኮባን ጓተማላ፣ እና ቴይለርስቪል ዩታሕ አመሰኛለሁ ውድ እህቶች፡፡ እነዚህን እቅዶች አቀባበል እና ለክብር መልሳችሁን ከልብ እናደንቃለን ።

በመጨረሻም ፤ በቤተመቅደስ ቡራኬ የተሰጣችሁን የክህነትን ሀይል እንድትረዱ እና በጌታ እና በእርሱ ሀይል ላይ ያላችሁን እምነትን በመለማመድ ያንን ሃይል እንድትጨምሩ በረከትን ልተውላችሁ እፈልጋለሁ ፡፡

ውድ እህቶች ፣ በጥልቅ አክብሮት እና አመስጋኝነት ፣ ለእናንተ ያለኝን ፍቅር እገልጻለሁ። እግዚአብሔር ህያው እንደሆነ በትህትና እመሰክራለሁ! ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህች የእርሱ ቤተክርስቲያን ናት። ይህንን የምመሰክረው ቅዱስ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፣ አሜን።”