አጠቃላይ ጉባኤ
መንገዱን አርቃችሁ ተመልከቱ
የጥቅምት 2021 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


መንገዱን አርቃችሁ ተመልከቱ

በጣም አስፈላጊ በሆኑ ነገሮች ላይ ማተኮር በተለይም “በመንገዱ በርቀት ላይ” ባሉ ዘላለማዊ በሆኑ ነገሮች ላይ ማተኮር በዚህ ሕይወት ውስጥ በብልሃት ለመንቀሳቀስ ቁልፍ ነው።

የ 15 ዓመት ልጅ ሳለሁ የተማሪ የመንጃ ፈቃድ አገኘሁ፣ ይህም ከወላጆቼ አንዳቸው ከእኔ ጋር ካሉ፣ መኪና እንድነዳ አስቻለኝ። አባቴ ለመንዳት እፈልግ እንደሆነ ሲጠይቀኝ በጣም ተደሰትኩ።

ጥቂት ማይሎች ያህል ከከተማው ወጣ ወዳለ፣ ውስን ሰዎች ወደሚጠቀሙበት ረጅምና ቀጥ ያለ ባለሁለት መስመር መንገድ ነዳ፤ ምናልባትም ይህ ቦታ አደጋን የማያስከትል ደህንነት ሊሚሰማው የሚችልበት ብቸኛው ቦታ ሊሆን እንደሚችል ልብ ሊባል ይገባል። በዋናው መንገድ ዳርቻ ላይ አቆመና፣ መቀመጫ ተቀያየርን። እሱም የተወሰኑ ስልጠናዎችን ሰጠኝ እና “አቁም እስክልህ ድረስ በመንገዱ ላይ ዘና በልና ንዳ” አለኝ።

የእሱን ትዕዛዞች በትክክል ተከተልኩ። ግን ከ 60 ሰከንዶች ገደማ በኋላ፣ እንዲህ አለ “ልጄ፣ መኪናውን ዳር አስይዝና አቁም። እንዲያቅለሸልሸኝ እያደረከኝ ነው። በመንገዱ ላይ በፍጥነት ወዲህ ወዲያ እያልክ ነው።” “ምን እያየህ ነው?“ ሲል ጠየቀ።

ትንሽ በስጨት ብዬ፣ “መንገዱን እያየሁ ነው” አልኩት።

ከዚያም እንዲህ አለ “ዓይኖችህን እያየሁ ነው፣ እናም ከመኪናው ኮፈን ፊት ለፊት ያለውን ብቻ ነው እየተመለከትክ ያለኸው። በቀጥታ ከፊትህ ያለውን ብቻ ከተመለከትክ በጭራሽ በቀጥታ መንዳት አትችልም። ” ከዚያ አፅንዖት በመስጠት፣ “መንገድህን አርቀህ ተመልከት። ይህም በቀጥታ እንድትነዳ ይረዳሃል። ”

እንደ የ15 ዓመት ልጅ፣ ያ ጥሩ የአነዳድ ትምህርት እንደሆነ አሰብኩኝ። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ያ ታላቅ የሕይወት ትምህርት እንደነበር ተረድቻለሁ። በጣም አስፈላጊ በሆኑ ነገሮች ላይ ማተኮር በተለይም “በመንገዱ በርቀት ላይ” ባሉ፣ ዘላለማዊ ነገሮች ላይ ማተኮር-በዚህ ሕይወት ውስጥ ለመንቀሳቀስ ቁልፍ ነው።

በአዳኙ ሕይወት ውስጥ በአንድ አጋጣሚ፣ ብቻውን ለመሆን ፈለገ፣ ስለዚህ “ለመጸለይ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ።” 1 ባሕሩን እንዲሻገሩ መመሪያ ሰጥቶ ደቀ መዛሙርቱን ላካቸው። በሌሊት ጨለማ ደቀ መዛሙርቱን የጫነችው መርከብ ኃይለኛ አውሎ ነፋስ አጋጠማት። ኢየሱስ እነሱን ለማዳን ባልተለመደ መንገድ ሄደ። የቅዱሳት መጻሕፍት ዘገባ እንዲህ ይላል፣ “ከሌሊቱ በአራተኛው ክፍል ኢየሱስ በባሕር ላይ እየተራመደ ወደ እነርሱ ሄደ።” 2 ባዩትም ጊዜ መፍራት ጀመሩ፣ ምክንያቱም ወደ እነርሱ እየቀረበ የነበረው ምስል የሆነ መንፈስ ወይም የሞተ ሰው ነፍስ መሰላቸው። ኢየሱስ ፍርሃታቸውን ተረድቶ አእምሮአቸውን እና ልባቸውን ለማረጋጋት ሲል “አይዞአችሁ፤ እኔ ነኝ፤ አትፍሩ።” አላቸው። 3

ጴጥሮስ እፎይታ ብቻ ሳይሆን ድፍረትም ተሰማው። ሁል ጊዜ ደፋር እና ብዙውን ጊዜ ችኩል የሆነው፣ ጴጥሮስ ወደ ኢየሱስ እንዲህ ሲል ጮኸ፣ “ጌታ ሆይ፣ አንተስ ከሆንህ በውሃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ። ” 4 ኢየሱስም በታዋቂውና ጊዜ በማይሽረው ግብዣው “ና።” አለው። 5

ጴጥሮስም በእርግጥ በጉጉት በመደሰቱ ከጀልባው ወደ ውሃው ውስጥ ሳይሆን ወደ ውሃው ላይ ወጣ። በአዳኙ ላይ ሲያተኩር፣ የማይቻለውን ማድረግ፣ እንዲያውም በውሃ ላይ መራመድ ቻለ። በመጀመሪያ፣ ጴጥሮስ በማዕበሉ አልተደናገጠም። ነገር ግን በመጨረሻ ላይ “በሃይለኛው” 6 ነፋስ ተዘናጋ እንዲሁም ትኩረቱን አጣ። ፍርሃቱም ተመለሰ። በውጤቱ እምነቱ እየቀነሰ መጣ፣ እናም መስመጥ ጀመረ። “ጌታ ሆይ አድነኝ ብሎ ጮኸ።” 7 ሁል ጊዜ ለማዳን የሚጓጓው አዳኝ እጁን ዘርግቶ ወደ ደህንነት ከፍ አደረገው።

ከዚህ ተዓምራዊ ዘገባ የምንማራቸው እጅግ ብዙ ትምህርቶች አሉ፣ ነገር ግን ሦስቱን እጠቅሳለሁ።

በክርስቶስ ላይ አትኩሩ

የመጀመሪያው ትምህርት፦በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ አተኩሩ። ጴጥሮስ ዓይኖቹ በኢየሱስ ላይ ባተኮሩ ጊዜ፣ በውሃ ላይ መራመድ ቻለ። ትኩረቱን በአዳኙ ላይ እስካደረገ ድረስ፣ ማዕበሉ፣ ወጀቡ፣ እና ንፋሱ ሊያደናቅፉት አልቻሉም።

የመጨረሻ ዓላማችንን መረዳታችን ትኩረታችን ምን መሆን እንዳለበት ለመወሰን ይረዳናል። ግቡን ሳናውቅ የተሳካ ጨዋታ መጫወት አንችልም፣ ዓላማውን ሳናውቅ ትርጉም ያለው ሕይወትም መኖር አንችልም። ሌሎች እንዳሉ ሆነው፣ ከተመለሰው የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ታላላቅ በረከቶች አንዱ “የሕይወት ዓላማ ምንድን ነው?” ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠቱ ነው። “በእዚህ ህይወት ያለን አላማ መደሰት እና ወደ እግዚአብሔር ፊት ለመመለስ መዘጋጀት ነው።” 8 ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ለመዘጋጀት እዚህ ምድር ላይ መሆናችንን ማስታወሳችን፣ ወደ ክርስቶስ በሚመሩን ነገሮች ላይ እንድናተኩር ይረዳናል።

በክርስቶስ ላይ ማተኮር ስነ ስርአትን ይጠይቃል፣ በተለይም የተሻለ ደቀ መዛሙርት እንድንሆን በሚረዱን ትንሽ እና ቀላል መንፈሳዊ ልምዶችን በተመለከተ። ያለ ስነ ስርአት ደቀመዝሙርነት የለም።

እኛ መሆን በምንፈልግበት ቦታ ላይ እንዲሁም ማን መሆን እንደምንፈልግ በመንገዱ ላይ አርቀን ስንመለከት እና እዚያ እንድንደርስ የሚረዱንን ነገሮች ለማድረግ በየቀኑ ስናገኝ በክርስቶስ ላይ ያለን ትኩረት የበለጠ ግልፅ ይሆናል። በክርስቶስ ላይ ማተኮር ውሳኔዎቻችንን ለማቅለል እና ጊዜያችንን እና ሀብቶቻችንን እንዴት በተሻለ ሁኔታ እንደምንጠቀም መመሪያን ሊሰጥ ይችላል።

የእኛን ትኩረት የሚጠይቁ ብዙ ነገሮች ቢኖሩም፣ ክርስቶስን ሁልጊዜ የትኩረታችን ማእከል የማድረግን አስፈላጊነት ከጴጥሮስ ምሳሌ እንማራለን። ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር መመለስ የምንችለው በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኘነት ብቻ ነው። በምንወድቅበት ጊዜ እንደ እርሱ ለመሆን እና የእርሱን ይቅርታ እና የማጠናከሪያ ሀይል ለመፈለግ ስንጥር በክርስቶስ ጸጋ እንመካለን።

ከሚያዘናጉ ነገሮች ተጠንቀቁ

ሁለተኛው ትምህርት ከሚያዘናጉ ነገሮች ተጠንቀቁ። ጴጥሮስ ትኩረቱን ከኢየሱስ አዙሮ ወደ ነፋሱ እና እግሩን በሚገፋው ማዕበል ላይ ሲያደርግ መስመጥ ጀመረ።

በክርስቶስ ላይ ከማተኮር እንዲሁም “በመንገዱ በርቀት ላይ ባሉ” ዘላለማዊ ነገሮች ላይ ትኩረታችንን ከማድረግ ሊከፋፍሉ የሚችሉ ብዙ ነገሮች “በኮፈኑ ፊት” አሉ። ዲያቢሎስ ትልቁ አዘናጊ ነው። ከታላቁ እና ሰፊው ህንፃ የሚመጡ ድምፆች እኛን ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ከምናደርገው ዝግጅት መንገድ አታለው ሊያስወጡን እንደሚፈልጉ ከሊሂ ሕልም እንማራለን። 9

ነገር ግን ያን ያህል ግልጽ ያልሆኑ አዘናጊዎች እንዲሁ አደገኛ ሊሆኑ ይችላሉ። “ክፋት እንዲያሸንፍ ብቸኛው አስፈላጊ ነገር መልካም ሰዎች ምንም አለማድረጋቸው ነው” እንደሚባለው ነው። ጠላት ጥሩ ሰዎች ምንም እንዳይሠሩ ወይም ቢያንስ ከፍ ካሉ ዓላማዎቻቸው እና ግቦቻቸው ይልቅ በሚያዘናጉ ነገሮች ላይ ጊዜያቸውን እንዲያባክኑ ለማድረግ የቆረጠ ይመስላል። ለምሳሌ፣ በመጠኑ ጤናማ የሆኑ ጊዜ ማሳለፊያዎች አንዳንድ ጊዜ ስነስርአት ከሌለ ጤናማ ወዳልሆኑ ማዘናጊያዎች ሊቀየሩ ይችላሉ። ትኩረትን የሚከፋፍሉ ነገሮች ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ የግድ መጥፎ ወይም ሥነ ምግባር የጎደላቸው መሆን እንደማይኖርባቸው ጠላት ያውቃል።

መዳን እንችላለን

ሶስተኛው ትምህርት፤ መዳን እንችላለን። ጴጥሮስ መስመጥ በጀመረ ጊዜ፣ “ጌታ ሆይ፣ አድነኝ ብሎ ጮኸ እናም ወዲያውም ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘው።” 10 እራሳችንን እየሰመጠን ካገኘን፣ መከራ ሲገጥመን ወይም ስንወድቅ፣ እኛም በእርሱ ልንታደግ እንችላለን።

በመከራ ወይም በፈተና ውስጥ፣ ማዳን ወዲያውኑ እንደሚመጣ ተስፋ በማድረግ እናንተም ልክ እንደ እኔ ልትሆኑ ትችላላችሁ። ነገር ግን አዳኙ ሐዋርያቱን ሊረዳ የመጣው ከለሊት በአራተኛው ሰዓት—አብዛኛውን ለሊት በማዕበል ሲደክሙ ከቆዩ በኋላ እንደሆነ አስታውሱ። 11 እርዳታው ወዲያውኑ ካልመጣ፣ ቢያንስ በምሳሌው ውሰጥ እንደተጠቀሰው ምሽት በሁለተኛው ሰዓት ወይም በሦስተኛው ሰዓት እንኳን እንዲመጣ ልንጸልይ እንችል ይሆናል። መጠበቅ በሚኖርብን ወቅት፣ ከአቅማችን በላይ መታገስ እንደሌለብን በማረጋገጥ አዳኝ ሁል ጊዜ እንደሚመለከት እርግጠኛ ሁኑ። 12 በሌሊት በአራተኛው ሰዓት ውስጥ ለምትጠባበቁ፣ ምናልባትም አሁንም በመከራ ውስጥ ላላችሁ፣ ተስፋ አትቁረጡ። በስጋዊ ህይወትም ሆነ በዘለአለም ህይወት ውስጥ፣ መዳን ሁል ጊዜ ለታማኞች ይመጣል።

አንዳንድ ጊዜ መስመጣችን የሚመጣው በስህተቶቻችን እና በመተላለፋችን ምክንያት ነው። በእነዚያ ምክንያቶች እራሳችሁን በመስመጥ ላይ ካገኛችሁ፣ ንስሐ ለመግባት አስደሳች ምርጫ አድርጉ። 13 ወደ እሱ የሚመለሱትን ወይም የሚመጡትን ከማዳን የላቀ ለአዳኝ የበለጠ ደስታ የሚሰጡ ነገሮች ጥቂት እንደሆኑ አምናለሁ። 14 ቅዱሳት መጻህፍት በአንድ ወቅት የወደቁ እና ጉድለት የነበራቸው ነገር ግን ንስሐ ገብተው በክርስቶስ እምነት በጸኑ ሰዎች ታሪኮች የተሞሉ ናቸው። እነዚያ ታሪኮች በቅዱሳት መጻህፍት ውስጥ ያሉበት ምክንያት፣ አዳኙ ለእኛ ያለውን ፍቅር እና እኛን የመዋጀት ኃይሉን ማለቂያ እንደሌለው ለማስታወስ እንደሆነ አስባለሁ። ንስሐ ስንገባ ደስ የሚለው አዳኙ ብቻ ሳይሆን እኛም ታላቅ ደስታን እንቀበላለን።

መደምደሚያ

“በመንገዱ ላይ አርቃችሁ ስትመለከቱ” አሳቢ እንድትሆኑ እና በእውነቱ አስፈላጊ በሆኑ ነገሮች ላይ ትኩረታችሁን እንድትጨምሩ እጋብዛችኋለሁ። ክርስቶስን የትኩረት ማእከላችን እናድርገው። በሚያዘናጉ ነገሮች ሁሉ፣ “ከኮፈኑ ፊት” ያሉት ነገሮች፣ እና በዙሪያችን በሚዞሩት ዐውሎ ነፋሶች መካከል፣ ኢየሱስ አዳኛችን እና ቤዛችን እንዲሁም ታዳጊችን መሆኑን እመሰክራለሁ። በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።