ቅዱሳት መጻህፍት
ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች ፻፴፪


ክፍል ፻፴፪

በናቩ ኢለኖይ ውስጥ በሐምሌ ፲፪፣ ፲፱፻፵፫ (እ.አ.አ.) የተመዘገበው፣ ስለአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን፣ በተጨማሪም የጋብቻ ቃል ኪዳን ዘለአለማዊነትን እና ደግሞም ከአንድ በላይ ሚስቶችን ስለማግባት መሰረታዊ መርሆ በሚመለከት በነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ በኩል የተሰጠ ራዕይ። ምንም እንኳን ይህ ራዕይ በ፲፰፻፵፫ (እ.አ.አ.) የተመዘገበ ቢሆንም፣ ከዚህ ራዕይ ጋር የተገናኙ አንዳንድ መርሆች ለነቢዩ ከ፲፰፻፴፩ (እ.አ.አ.) መጀመሪያ ጀምሮ ታውቀው ነበር። አስተዳደሪያዊ አዋጅ ፩ን ተመልከቱ።

፩–፮፣ ዘለአለማዊ ክብር የሚገኘው በአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ነው፤ ፯–፲፬፣ የዚህ ቃል ኪዳን ምልክት እና ቅድመ ሁኔታዎች ተሰጥተዋል፤ ፲፭–፳፣ ሰለስቲያል ጋብቻ እና የቤተሰብ ስብስብ ቀጣይነት ሰዎች አማልክት እንዲሆኑ ያስችላቸዋል፤ ፳፩–፳፭፣ ቀጭኑ እና ጠባቡ መንገድ ወደዘለአለም ህይወት ይመራል፤ ፳፮–፳፯፣ መንፈስ ቅዱስን መስደብ በሚመለከት ህግ ተሰጠ፤ ፳፰–፴፱፣ የዘለአለማዊ እድገት እና ዘለአለማዊ ክብር ቃል ኪዳን ለሁሉም ዘመን ነቢያት እና ቅዱሳን ተደርገዋል፤ ፵–፵፯፣ ጆሴፍ ስሚዝ በምድር ላይ እና በሰማይ ውስጥ ለማሰር እና ለማተም ሀይል ተሰጠው፤ ፵፰–፶፣ ጌታ በእርሱ ላይ ዘለአለማዊ ክብር አተመበት፤ ፶፩–፶፯፣ ኤማ ስሚዝ ታማኝ እና እውነተኛ እንድትሆን ተመከረች፤ ፶፰–፷፮፣ ከአንድ በላይ የሆኑ ሚስቶችን ስለማግባት የሚመሩ ህግጋት ተሰጥተዋል።

በእውነትም ለአንተ አገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ጌታ እንዲህ ይላል፣ እኔ ጌታ አገልጋዮቼን አብርሐምን፣ ይስሀቅን፣ እና ያዕቆብን፣ ደግሞም ሙሴን፣ ዳዊትን፣ እና ሰለሞንን ብዙ ሚስቶችና ዕቁባቶች የነበሯቸውን መሰረታዊ መርሆች እና ትምህርቶችን በሚመለከት እንዴት ከጥፋት ነጻ እንዳደረኳቸው እንዲገባህ እና ለማወቅ ከእጄ እንደጠየከኝ—

እነሆ፣ እና አስተውል፣ እኔ ጌታ አምላክህ ነኝ፣ እና ይህን ጉዳይ በሚነካም መልስን እሰጥሀልሁ።

ስለዚህ፣ ልሰጥህ ያሉትን መመሪያዎች ለመቀበል እና ለማክበር ልብህን አዘጋጅ፤ ይህ ህግ ለተገለጠላቸው ሁሉ ይህን ማክበር አለባቸውና።

እነሆ፣ አዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ገልጬላችኋለሁና፤ እና ይህን ቃል ኪዳን ካልኖራችሁበት፣ ከዚያ የተኮነናችሁ ናችሁ፣ ማንም ይህን ቃል ኪዳን ሊቃወምና እና ወደ ክብሬ ይገባ ዘንድ አይችልምና።

ከእጄ በረከት የሚያገኙም ለዚያ በረከት የተመደበውን ህግና አለም ከመመስረቷም በፊት በስራ ላይ የዋሉትን ቅድመ ሁኔታ ሊኖሩባቸው ያስፈልጋቸዋልና።

እና አዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳንን በሚመለከት፣ በስራ ላይ የዋለው ለክብሬ ሙላት ነበር፤ እና ይህን ሙላት የሚቀበል በህጉ ይኑር እና መኖርም አለበት፣ ወይም ይኮነናል፣ ይላል ጌታ አምላክ።

እና እውነት እላችኋለሁ፣ የዚህ ህግ ቅድመ ሁኔታዎች እነዚህ ናቸው፥ በተቀባው፣ ለጊዜ እና ለዘለአለም፣ በዚህ ምድር ይህን ሀይል እንዲይዝ በመደብኩት (እና አገልጋዬ ጆሴፍን ይህን ሀይል በመጨረሻ ቀናት እንዲይዝ መድቤአለሁ እና የዚህ ክህነት ሀይል እና ቁልፎች ይሰጠው ዘንድ የተገባ ከአንድ በላይ የለም) በእኔ በተቀባው በኩል በራዕይ እና በትዕዛዝ እና ከሁሉም በላይ በሆነ የቅዱስ ተስፋ መንፈስ ያልተሰሩ፣ ያልገቡና ያልታተሙ ቃል ኪዳናት፣ ስምምነቶች፣ የተፈረመባቸው መረጃዎች፣ ግዴታዎች፣ መሀላዎች፣ ስዕለቶች፣ ግንኙነቶች፣ ተባባሪነቶች፣ ወይም የሚጠበቅባቸው፣ በሙታን ትንሳኤ እና በኋላም ሁሉም ፍቱንነት፣ መልካምነት፣ ወይም ሀይል አይኖራቸውም፤ ለዚህም ውጤት ያልተገቡ ስምምነቶች ሰዎች በሞቱ ጊዜ መጨረሻው ይሆናል።

እነሆ፣ ቤቴ የስርዓት ቤት ነው፣ ይላል ጌታ አምላክ፣ እና የግራ መግባት ቤት አይደለም።

በስሜ ያልተደረጉትን መስዋዕቶችን እቀበላለሁን? ይላል ጌታ።

ወይም ያልመደብኩትን ከእጆቻችሁ እቀበላለሁን?

፲፩ እና እንዲሁም እኔ እና አባቴ ለእናንተ ከዚህ አለም በፊት እንደሾምነው፣ በህግ ካልሆነ በስተቀር፣ ይላል ጌታ፣ እመድብላችኋለሁን?

፲፪ እኔ ጌታ አምላካችሁ ነኝ፤ እና ይህን ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ—በእኔ እና ህጌ በሆነው በቃሌ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም፣ ይላል ጌታ።

፲፫ እና በአለም ያለው ሁሉም ነገር፣ በሰዎችም፣ ዙፋናት ወይም በጌትነት ወይም በአለቅነት ወይም በሥልጣናት ስም ባላቸው ነገሮች የተመደበ ቢሆንም፣ ምንም ቢሆኑ፣ በእኔ ወይም በቃሌ ካልሆኑ ይጣላሉ፣ ይላል ጌታ፣ እና ሰዎች ከሞቱም በኋላ፣ ወይም በትንሳኤ ወይም በኋላም እንዲሁ አይቀሩም፣ ይላል ጌታ አምላካችሁ።

፲፬ የሚቀሩትም ማናቸውም ነገሮች በእኔ ናቸው፤ እና በእኔ ያልሆኑትም ማናቸውም ነገሮች ይናወጣሉ እናም ይደመሰሳሉ።

፲፭ ስለዚህ፣ ሰው በአለም ውስጥ ሚስት ቢያገባ፣ እና በእኔ ወይም በቃሌ ባያገባት፣ እና በአለም እስካለም ድረስ ከእርሷ ጋር እና እርሷም ከእርሱ ጋር ቃል ኪዳን ቢገቡ፣ ሲሞቱና ከአለም ሲለዩ ቃል ኪዳናቸውና ጋብቻቸው ሀይል አይኖራቸውም፤ ስለዚህ፣ ከአለም ሲለዩ በምንም ህግ አይታሰሩም።

፲፮ ስለዚህ፣ ከአለም ሲለዩ አያገቡም ወይም አይጋቡምም፤ ነገር ግን በሰማይ ውስጥ እንደ መላእክት ይመደባሉ፣ እነዚህም መላእክት ከዚህም በላይ፣ እና በክብርን በዘለአለም እድገት ከሁሉ ይልቅ ብቁ ለሆኑት ረጂ አገልጋዮች ናቸው።

፲፯ እነዚህ መላእክት በህጋቴ አልኖሩምና፤ ስለዚህ፣ ሊያድጉ አይችሉም፣ ነገር ግን ተለያይተው እና በብቸኝነት፣ ከፍ ሳይደረጉ፣ በዳኑበት ሁኔታ ዘለአለማዊ ክብር ሳይኖራቸው ይቆያሉ፤ እና ከዚያም ጊዜ ጀምሮ አማልክት አይደሉም፣ ነገር ግን ለዘለአለም የእግዚአብሔር መላእክት ናቸው።

፲፰ ደግሞም፣ እውነት እላችኋለሁ፣ ሰው ሚስት ቢያገባ፣ እና ለጊዜ እና ለዘለአለም ቃል ኪዳን ቢያደርግ፣ ያም ቃል ኪዳን በእኔ ወይም ህጌ በሆነው በቃሌ ባይጸና እና ለዚህ ሀይል በቀባሁት እና በመደብኩት በኩል በቅዱስ የተስፋ መንፈስ ያልታተመ ቢሆን፣ ከዚያም ከዚህ አለም ሲለዩ ጋብቻቸው ተቀባይነት ወይም ሀይል የለውም፣ ምክንያቱም በእኔ ወይም በቃሌ አልተሳሰሩምና፣ ይላል ጌታ፤ ከአለም ሲለዩም በዚያም ተቀባይነት አያገኝም ምክንያቱም በዚያ ሊያልፏቸው የማይችሉ መላእክት እና አማልክት ተመድበዋልና፤ ስለዚህ ክብሬን መውረስ አይችሉም፤ ቤቴ የስርዓት ቤት ነውና፣ ይላል ጌታ አምላክ።

፲፱ ደግሞም፣ እውነት እላችኋለሁ፣ ህጌ በሆነው በቃሌ እንዲሁም በአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ሰው ሚስትን ቢያገባ፣ እና ይህም በተቀባው፣ የዚህን ሀይል እና የዚህን ክህነት ቁልፎች በመደብኩለት አማካይነት፣ በቅዱስ የተስፋ መንፈስ ይታተማል፤ እናም ለእነርሱም እንዲህ ይባላል—እናንተ በመጀመሪያው ትንሳኤ ትመጣላችሁ፤ እና ከመጀመሪያው ትንሳኤ በኋላም ቢሆን፣ በሚቀጥለው ትንሳኤ፤ እና ዙፋናት፣ መንግስታት፣ ጌትነቶች፣ እና ሀይላት፣ አለቅነት፣ ሁሉንም ከፍታና ዝቅታን ይወርሳሉ—ከዚያም በበጉ የህይወት መፅሀፍ ውስጥ ንጹህ ደም የማይፈስበት ግድያን እንደማይፈፅም ይጻፋል፣ እና በቃል ኪዳኔ ብትኖሩ፣ እና ንጹህ ደም የሚያፈስበትን ግድያ ባትፈጸሙ፣ በጊዜ እና በዘለአለም ሁሉ አገልጋዬ በእነርሱ ላይ የሚኖረው ማንኛውም ነገሮች ሁሉ ይደረጉላቸዋል፤ እና ከዚህ አለም ሲለዩም ሙሉ ሀይል ያለው ይሆናል፤ እና በዚያ በተቀመጡት በመላእክት እና አማልክት አልፈው፣ በራሳቸው ላይ እንደታተሙት በሁሉም ነገሮች ወደ ዘለአለማዊ ክብር እና ወደ ክብራቸው ይሄዳሉ፣ ይህም ክብር ለዘለአለም የሙላት እና ለዘራቸውም ቀጣይነት ያለው ይሆናል።

ከዚያም እነርሱም አማልክት ይሆናሉ፣ ምክንያቱም መጨረሻ የላቸውምና፤ ስለሚቀጥሉም፣ በዚህም ከዘለአለም ወደዘለአለም የሚኖሩ ይሆናሉ፤ ከዚያም ሁሉም ነገሮች ለእነርሱ ተገዢ ስለሚሆኑ፣ ከሁሉም በላይ ይሆናሉ። ከዚያም ሁሉም ሀይል ስለሚኖራቸው፣ አማልክት ይሆናሉ፣ እና መላእክትም ተገዢ ይሆኑላቸዋል።

፳፩ እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ በህጌ ካልኖራችሁ በስተቀር ይህን ክብር አታገኙም።

፳፪ ወደ ዘለአለማዊ ክብር እና ወደ ቀጣይ ህይወት መቀጠል የሚወስደው ደጅ የጠበበመንገዱም የቀጠነ ነውና፣ የሚያገኙትም ጥቂቶች ናቸው፣ በዚህ አለም ስላልተቀበላችሁኝ አታውቁኝም።

፳፫ ነገር ግን በዚህ አለም ብትቀበሉኝ፣ ከዚያም ታውቁኛላችሁ፣ እና ዘለአለማዊ ክብራችሁንም ትቀበላላችሁ፤ እኔ ባለሁበት እናንተም ደግሞ ትሆናላችሁ።

፳፬ እውነተኛ እና የጥበብ አምላክ ብቻ የሆነውንና የላከውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘለአለም ሕይወት ናት። እኔም እርሱ ነኝ። ስለዚህ ህጌን ትቀበላላችሁ።

፳፭ ወደ ሞት የሚመራው ደጅ ሰፊ፣ እናም መንገዱም የሰፋ ነውና፤ ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው፣ ምክንያቱም አይቀበሉኝም ወይም በህጌም አይኖሩምና።

፳፮ እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ ሰው በቃሌ መሰረት ሚስት ቢያገባ፣ እና እኔም በመደብኩት መሰረት በቅዱስ የተስፋ መንፈስ ቢታተሙ፣ እና እርሱ ወይም እርሷ በአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ላይ ምንም ኃጢአት ወይም መተላለፍ እና ሁሉንም አይነት መተላለፍ ባያደርጉ እና ንጹህንም ደም ለማፍሰስ ባይገድሉ፣ በመጀመሪያው ትንሳኤ ይመጣሉ፣ እና ወደ ዘለአለማዊ ክብራቸውም ይገባሉ፤ ነገር ግን በስጋቸው የወደቁ ይሆናሉ፣ እና እስከቤዛም ቀን በሰይጣን እንዲጎሰሙ ይሰጣሉ፣ ይላል ጌታ።

፳፯ መንፈስ ቅዱስን መሳደብ ግን በዚህ ዓለም ቢሆን ወይም በሚመጣው ስርየት የለውም፣ በዚያም አዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳኔን ከተቀበላችሁ በኋላ ንጹህን ደም በማፍሰስ የምትገድሉበት፣ እና በሞቴም የምትስማሙበት ነው፤ እና በዚህ ህግ የማይኖር ማንም ወደ ክብሬ ሊገባ አይችልም፣ ነገር ግን ይኮነናል፣ ይላል ጌታ።

፳፰ እኔ ጌታ አምላክህ ነኝ፣ እና ለአንተም ከአለም ፍጥረት በፊት በእኔ እና በአባቴ እንደተመደበ፣ የቅዱስ ክህነቴን ህግ እሰጥሀለሁ።

፳፱ አብርሐም በራዕይ እና ትእዛዝ፣ በቃሌ የተቀበለውን ሁሉንም ነገሮች ተቀበለ፣ እና ወደ ዘለአለማዊ ክብሩም ገብቷል እና በዙፋኑም ተቀምጧል ይላል ጌታ።

አብርሐም ስለዘሩ እና ስለወገብም ፍሬው በሚመለከት ቃል ኪዳንን ተቀበለ—ከእርሱም ወገብ፣ በስምም ከአገልጋዬ ዮሴፍ የመጣህ ነህ—እነዚህም በአለም ውስጥ እስከሚገኑ ድረስ ይቀጥላሉ፤ እና አብርሐምን እና ዘሩን በሚመለከት፣ ከአለም ውጪም ይቀጥላሉ፤ በአለም ውስጥ እና ከአለም ውጪም እንደ ከዋክብት በዝተውም ይቀጥላሉ፤ ወይም፣ በባህር ዳር ያለን አሸዋ ብትቆጥርም እነርሱን ልትቆጥራቸው አትችልም።

፴፩ ይህም ቃል ኪዳን ያንተም ነው፣ ምክንያቱም አንተ ከአብርሐም ነህና፣ እና ቃል ኪዳኑም ለአብርሐም ተሰርቶ ነበርና፤ እና በዚህ ህግም የአባቴ ስራ ይቀጥል ዘንድ፣ በዚህም እራሱን ያከብር ዘንድ ነው።

፴፪ ስለዚህ ሂድ እና የአብርሐምን ስራዎች አድርግ፤ ወደህጌም ግባ እናም ትድናለህ።

፴፫ ነገር ግን ወደ ህጌ ባትገባ ለአብርሐም የተገባውን የአባቴን ቃል ኪዳን አትቀበልም።

፴፬ እግዚአብሔር አብርሐምን አዘዘው እና ሳራ ለአብርሐም አጋርን ሚስት ትሆነው ዘንድ ሰጠችው። እና ይህን ለምን አደረገች? ምክንያቱም ይህም ህግ ነበር፤ እና ከአጋርም ብዙ ህዝብ ወጣ። ስለዚህ ይህም፣ ከሌሎች ነገሮች ጋር፣ ቃል ኪዳኖችን ያሟላ ነበር።

፴፭ ስለዚህ አብርሐም በኩነኔ ላይ ነበር? እውነት እላችኋለሁ፣ አልነበረም፤ እኔ ጌታ ይህን አዝዤአለሁና

፴፮ አብርሐም ልጁን ይስሀቅን ለመስዋዕት እንዲያቀርብ ታዝዞ ነበር፤ ይሁን እንጂ፣ አትግደል ተብሎ ተፅፎ ነበር። አብርሐም ግን እምቢ አላለም፣ እና ይህም እንደፅድቅ ተቆጠረለት።

፴፯ አብርሐም እቁባቶችን ተቀበለ፣ እና እነርሱም ልጆችን ወለዱለት፤ እና ይህም ለእርሱ እንደፅድቅ ተቆጥሮለታል፣ ምክንያቱም ለእርሱ ተሰጥተዋልና፣ እና በህጌም ኖሯል፤ ይስሀቅ እና ያዕቆብም ከታዘዟቸው ነገሮች በስተቀር ምንም ሌላ ነገርን አላደረጉም፤ እና ከታዘዙትም ነገር ውጪ ምንም ሌላ ነገርን ስላላደረጉ፣ በቃል ኪዳኖች መሰረት ወደ ዘለአለማዊ ክብራቸው ገብተዋል፣ እና በዙፋናትም ተቀምጠዋል፣ እና መላእክት ሳይሆኑ አማልክት ናቸው።

፴፰ ዳዊትም ብዙ ሚስቶች እና እቁባቶችን ተቀበለ፣ እና ከፍጥረት መጀመሪያ እስከዚህ ጊዜ ድረስ አገልጋዮቼም ሰለሞን እና ሙሴ፣ እና ብዙ ሌሎች አገልጋዮቼም ደግመው ተቀበሉ፤ እና ከእኔም ዘንድ ካልተቀበሏቸው ነገሮች በስተቀር፣ በምንም ኃጢአትን አልሰሩም።

፴፱ የዳዊት ሚስቶች እና እቁባቶች በአገልጋዬ በናታን እጅ እጅ እና የዚህ ሀይል ቁልፍ በተሰጣቸው በሌሎች ነቢያት እጅ አማካይነት ለእርሱ የተሰጡት ከእኔ ዘንድ ነበር፤ እና ከኦርዮ እና ሚስቱ ጉዳይ በስተቀር በእነዚህ ነገሮች በእኔ ላይ ምንም ኃጢአት አልሰራም፤ ስለዚህ ከዘለአለማዊ ክብሩም ወድቋል፣ እና የድርሻውንም ተቀብሏል፤ እና እነዚህንም ከዚህ አለም ውጪ አይወርሳቸውም፣ ለሌላ ሰጥቻቸዋለሁና፣ ይላል ጌታ።

እኔ ጌታ አምላካችሁ ነኝ፣ እና ለአንተ ኣገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ ሁሉንም ነገሮች ዳግም ትመልስ ዘንድ ሀላፊነት ሰጥቼሀለሁ። ያሻህንን ጠይቅ፣ እና በቃሌም መሰረት ይሰጥሀል።

፵፩ እና ስለ ማመንዘር ስለጠየቅህ፣ እውነት፣ እውነት እልሀለሁ፣ ሰው በአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ሚስትን ቢቀበል፣ እና እርሷም በቅዱስ ቅባት ካልመደብኩላት ከሌላ ሰው ጋር ብትገኝ፣ አመንዝራለች፣ እና ትጠፋለች።

፵፪ በአዲስ እና ዘለአለማዊ ቃል ኪዳን ውስጥ ካልሆነች፣ እና ከሌላ ሰውም ጋር ብትሆን፣ አመንዝራለች

፵፫ እና ባሏ ከሌላ ሴት ጋር ቢሆን፣ እና በመሀላም ላይ ቢሆን፣ መሀላውን ሰብሯል እና አመንዝሯል።

፵፬ እና እርሷ ካላመነዘረች፣ ነገር ግን ንጹህ ብትሆንና መሀላዋን ባትሰብር፣ እና ብታውቅም፣ እና እኔም ለአንተ ለአገልጋዬ ጆሴፍ ብትገልጥልህ፣ ከዚያም በቅዱስ ክህነት ስልጣን ሀይል መሰረት እርሷን ለመውሰድ እና ላላመነዘረው፣ ነገር ግን ታማኝ ለሆነው ትሰጥ ዘንድ ሀይል አለህ፤ እርሱ በብዙዎች ላይ ገዢ ይሆናልና።

፵፭ የክህነትን ቁልፎችና ሀይል በላይህ አድርጌአለሁ፤ በዚህም ሁሉንም ነገሮች ዳግም እመልሳለሁ፤ በጊዜውም ሁሉንም ነገሮች አሳውቅሀለሁ።

፵፮ እና እውነት፣ እውነት እልሀለሁ፣ በምድር የምታትመው ሁሉ በሰማይ ይታተማል፤ እና በስሜ እና በቃሌ በምድር የምታሰረው ሁሉ በሰማያት ለዘለአለም ይታሰራል፣ ይላል ጌታ፤ በምድር ላይ የምትሰርዘው ኃጢአት ሁሉ በሰማይ ለዘለአለም ይሰረዛል፤ እና በምድር ላይ የምትይዘው ኃጢአት ሁሉ በሰማይ ለዘለአለም ይያዛል።

፵፯ ደግሜም፣ እውነት እላለሁ፣ የምትባርከውን ማንኛውንም እባርካለሁ፣ እና የምትረግመውን ማንኛውንም እረግማለሁ፣ ይላል ጌታ፤ እኔ ጌታ አምላክህ ነኝና።

፵፰ ደግሞም፣ አገልጋዬ ጆሴ እውነት እልሀለሁ፣ በምድር የምትሰጠው ማንኛውም ነገር፣ እና ለማንም በቃሌ እና በህጌ መሰረት ማንንም በምድር ላይ ምንም ብትሰጥ፣ ይህንም በእርግማን ሳይሆን በበረከት በሀይሌ እጎበኘዋለሁ፣ ይላል ጌታ፣ እና በምድር እና በሰማይ ያለኩነኔ ይሆናል።

፵፱ እኔ ጌታ አምላክህ ነኝ፣ እና እስከ አለም መጨረሻ ድረስ እና ለዘለአለም ሁሉ ከአንተ ጋር እሆናለሁና፤ በእውነትም ዘለአለማዊ ክብርህን አትምብሀለሁ፣ እና በአባቴ መንግስት ውስጥ ከአባትህ አብርሐም ጋር ዙፋንን አዘጋጅልሀለሁና።

እነሆ፣ መስዋዕቶችህን አይቻለሁ፣ እና ኃጢአቶችህንም ሁሉ እሰርያለሁ፤ ለነገርኩህ ለዚያ ታዛዥ በመሆን ያደረግኸውን መስዋዕትነት አይቻለሁ። ስለዚህ ሂድ፣ እና አብርሐም ልጁን ይስሀቅን ለመስዋዕት ያቀረበውን እንደተቀበልኩኝ፣ የምታመልጥበትንም መንገድ አዘጋጅቼአለሁ።

፶፩ እውነት እልሀለሁ፥ ለአንተ ለሚስትነት የሰጠሁህን ባሪያዬ ኤማ ስሚዝ ትረጋጋ ዘንድ እና እንድትሰጣትም ካዘዝኩህ በላይ እንዳትቀበል ትእዛዝን እሰጣታለሁ፤ ለአብርሐም እንዳደረግሁት፣ ለሁላችሁንም ለማረጋገጥ፣ እና ከእጆቻችሁ በቃል ኪዳን እና በመስዋዕት መስዋዕትን ለመጠየቅ ይህን አድርጌአለሁና ይላል ጌታ።

፶፪ እና አገልጋዬ ኤማ ስሚዝ ለአገልጋዬ ጆሴፍ ስሚዝ የተሰጡትን፣ በፊቴ ሰጋ ያላቸውና ንጹህ የሆኑትን ነገሮች ሁሉ ትቀበል፤ እና ንጹህ ያልሆኑት፣ እና ንጹህ ነን የሚሉት፣ ይጠፋሉ፣ ይላል ጌታ አምላካችሁ።

፶፫ እኔ ጌታ አምላክሽ ነኝና፣ እና ድምጼንም አክብሪ፤ እና ለአገልጋዬ ጆሴፍም በብዙ ነገሮች ገዢ ይሆን ዘንድ ሰጥቼዋለሁ፤ በትንሽ ነገሮች ታማኝ ሆኗልና፣ እና ከዚህም ጊዜ ጀምሮ አበረታዋለሁ።

፶፬ እና ባሪያዬን ኤማ ስሚዝን ከአገልጋዬ ጆሴፍ ጋር እንድትኖር እና ከአገልጋዬ ጆሴፍ በስተቀር ከማንም ጋር እንዳትጣመር አዝዣታለሁ። ነገር ግን በዚህ ትእዛዝ ባትኖር ትጠፋለች፣ ይላል ጌታ፤ እኔ አምላክሽ ነኝ፣ እና በህጌም ባትኖር አጠፋታለሁ።

፶፭ ነገር ግን በዚህ ህግ ባትኖር፣ ከዚያም አገልጋዬ ጆሴፍ ሁሉንም ነገሮች፣ እንዲሁም እንዳለው፣ ለእርሷ ያድርግ፤ እና እኔም እባርከዋለሁ እናም አባዛዋለሁም እና ለእርሱም በዚህ አለም አባቶችና እናቶች፣ ወንድሞችና እህቶች፣ ቤቶችና መሬቶች፣ ሚስቶችና ልጆች በመቶ እጥፍ፣ እና በዘለአለምም አለማት የዘለአለም ህይወትን አክሊል እሰጠዋለሁ።

፶፮ ደግሞም፣ እውነት እላለሁ፣ ገረዴ አገልጋዬን ጆሴፍ ለተላለፋቸው ይቅርታ ትስጠው፤ እና ከዚያም በእኔ ላይ በመተላለፍ ለተላለፈችው ይቅርታ ይሰጣታል፤ እና እኔ ጌታ አምላካችሁ እባርካታለሁ፣ እናም አባዛታለሁ፣ እና ልቧንም እንዲደሰት አደርጋለሁ።

፶፯ ደግሞም፣ እላለሁ፣ ጠላት መጥቶ እናም እንዳያጠፋውም፣ አገልጋዬ ጆሴፍ ንብረቱን ከእጆቹ አያውጣ፣ ሰይጣን ለማጥፋት ይፈልጋልና፤ እኔ ጌታ አምላክህ ነኝ፣ እና እርሱም አገልጋዬ ነውና፤ እና እነሆ፣ አስተውሉም፣ እኔ ከአባታችሁ አብርሐም ጋር፣ እስከ ዘለአለማዊ ክብሩ እንደነበርኩኝ፣ ከእርሱም ጋር ነኝ።

፶፰ አሁን፣ የክህነት ህግን በሚመለከት፣ ይህን የሚመለከቱ ብዙ ነገሮች አሉ።

፶፱ እውነት፣ ሰው በአባቴ እንደ አሮን በድምጼ፣ እና በላከኝም ድምፅ፣ ቢጠራ እና እነዚህንም የክህነት ቁልፎች ባበረክትለት፣ በስሜ፣ በህጌና በቃሌ ምንም ነገንር ቢያደርግ፣ ምንም ኃጢአትን አይሰራም፣ እና እኔም ከጥፋት ነጻ አደርገዋለሁ።

ስለዚህ ማንም አገልጋዬ ጆሴፍን አያጥቃ፤ እኔ ከጥፋት ነጻ አደርገዋለሁና፤ ለተላለፋቸው ከእጆቹ የምጠብቃቸውን መስዋዕቶች ያደርጋልና፣ ይላል ጌታ አምላካችሁ።

፷፩ ደግሞም፣ የክህነት ህግን በሚመለከት—ማንም ሰው ድንግልን ቢያገባ፣ እና ሌላን ለማግባት ፍላጎት ቢኖረው፣ እና የመጀመሪያዋም ፈቃዷን ብትሰጥ፣ እና ሁለተኛይቱን ቢያገባ፣ እና እነርሱም ድንግል ቢሆኑ፣ እና ለሌላም ሰው መሀላ ባይገቡ፣ እርሱም አያጠፋም፤ እርሱም አያመነዝርም ምክንያቱም ለእርሱ ተሰጥተውታልና፤ ከእርሱ በቀር ለማንም ካልሆኑት ጋር አያመነዝርምና።

፷፪ በዚህ ህግ አስር ድናግል ቢሰጡትም፣ ሊያመነዝር አይችልም፣ የእርሱ ናቸውና፣ እና ለእርሱም ተሰጥተውታልና፤ ስለዚህ አይጠፋም።

፷፫ ነገር ግን አንድ ወይም ከአስር ደናግላን አንዷ ካገባች በኋላ ከሌላም ወንድ ጋር ብትሆን፣ አመንዝራለች እና ትጠፋለችም፤ እነርሱም የሰው በትእዛዜ መሰረት ነፍሳትን እንዲወልዱ፣ እና ከአለም መመስረት በፊት በአባቴ የተሰጠውን ቃል ኪዳን ለማሟላት፣ እና በዘለአለሙም አለማት ዘለአለማዊ ክብራቸው እንዲበዛና ምድርን እንዲሞላ የተሰጡት ናቸውና፤ ይህም ይከበር ዘንድ የአባቴ ስራ የሚቀጥልበት ነውና።

፷፬ ደግሞም፣ እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ የዚህን ሀይል ቁልፍ የያዘ ማንም ሰው ሚስት ቢኖረው፣ እና እነዚህን ነገሮች በሚመለከት የክህነቴን ህግ ቢያስተምራት፣ ከዚያም እርሷም ትመነው እናም ትደግፈው፣ ወይም ትጠፋለች፣ ይላል ጌታ አምላካችሁ፤ እኔ አጠፋታለሁና፤ ህጌን የሚቀበሉ እና በህጌም የሚኖሩትን ሁሉ አጎላቸዋለሁና።

፷፭ ስለዚህ፣ ስላላመነች እና በቃሌ መሰረት ስላልረዳችው፣ ይህን ህግ ባትቀበል፣ እኔ ጌታ የምሰጠውን ማንኛዎቹን ነገሮች ሁሉ ለመቀበል ይህም በእኔ ዘንድ እንደ ህግ ይሆናል፤ እና ከዚያም እርሷም ህግ ተላላፊ ትሆናለች፤ እና እርሱም አብርሐም አጋርን እንዲያገባ ባዘዝኩት ጊዜ ለአብራም በህጉ መሰረት ከደገፈችው ከሳራ የህግ ግዴታ ነጻ ነው።

፷፮ አሁንም፣ ይህን ህግ በሚመለከት፣ እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ ከዚህ በኋላ ተጨማሪን ነገር እገልጥላችኋለሁ፤ ስለዚህ፣ ለጊዜው ይህ ይብቃ። እነሆ፣ እኔ አልፋና ኦሜጋ ነኝ። አሜን።