ቅዱሳት መጻህፍት
ሔለማን ፲፭


ምዕራፍ ፲፭

ጌታ ኔፋውያንን የሚገስጻቸው ስለሚወዳቸው ነው—የተለወጡ ላማናውያን በእምነታቸው ፅኑ እንዲሁም የማይነቃነቁ ናቸው—ጌታ በኋለኛው ቀናት ለላማናውያን መሃሪ ይሆናል። በ፮ ም.ዓ. ገደማ።

እናም እንግዲህ፣ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ፣ እነሆ፣ ንስሃ ካልገባችሁ ቤታችሁ እንደሚወድምባችሁ እናገራለሁ።

አዎን፣ ንስሃ ካልገባችሁ፣ ሴቶቻችሁ በሚያጠቡበት ቀን የሚያዝኑበት ታላቅ ምክንያት ይኖራቸዋል፤ ምክንያቱም ለመሸሽም ትሞክራላችሁ እናም የምትሰደዱበት ስፍራ አይኖራችሁም፤ አዎን፣ ለእርጉዞች ወዮላቸው፣ እነርሱም ከባድ ይሆናሉ እናም መሸሽም አይችሉምና፤ ስለዚህም ይረገጣሉ እናም እንዲጠፉም ወደኋላ ይቀራሉ።

አዎን፣ የኔፊ ህዝብ ተብለው ለሚጠሩት እነዚህን ሁሉ ምልክቶች እናም አስደናቂ ነገሮች በሚመለከቱበት ጊዜ ንስሃ ካልገቡ ወዮላቸው፤ እነሆም፣ በጌታ የተመረጡ ህዝቦች የነበሩ ናቸውና፤ አዎን፣ የኔፊን ህዝብ ወዷቸዋል እናም ደግሞ ገስጿቸዋል፤ አዎን፣ ስለሚወዳቸው በክፋታቸው ዘመን ቀጥቷቸዋል።

ነገር ግን እነሆ ወንድሞቼ ላማናውያን ስራቸው ያለማቋረጥ ክፉ ስለነበር ጠልቷቸው ነበር፣ እናም ይህም የሆነበት በአባቶቻቸው ወግ ክፋት የተነሳ ነበር። ነገር ግን እነሆ፣ ደህንነት ግን በኔፋውያን ስብከት የተነሳ መጥቶላቸዋል፤ እናም ለዚህም አላማ ጌታ ቀናቸውን አርዝሞላቸዋል

እናም አብዛኞቹ ክፍሎች በተወሰነላቸው ጎዳና እንደሚንቀሳቀሱ ልብ እንድትሉ እፈልጋለሁ፣ በእግዚአብሔርም ፊት በጥንቃቄ ይራመዳሉ፤ እናም በሙሴ ህግ መሰረትም ትዕዛዛቱንና ህግጋቱን እንዲሁም ፍርዱን ያከብራሉ።

አዎን፣ እንዲህ እላችኋለሁ፣ አብዛኞቹ ይህንን ያደርጋሉ፤ እናም የተቀሩት ወንድሞቻቸውን ወደ እውነት ያመጡ ዘንድም ያለማቋረጥ ትጋትን ያደርጋሉ፤ ስለሆነም በየቀኑም ቁጥራቸውን ከፍ የሚያደርጉ ብዙዎች አሉ።

እናም እነሆ፣ እናንተ በእራሳችሁ እንደምታውቁት፣ ምስክር ሆናችሁበታልና፣ ብዙዎች ወደ እውነት እውቀት የመጡት፣ እናም ክፉውንና የረከሰውን የአባቶቻቸውን ወግ ያውቁትና፣ ቅዱሳት መጻሕፍትንም እንዲያምኑ፤ አዎን፣ እምነትና ንስሃም በልባቸው ለውጥን ስለሚያመጣላቸው ስለተፃፉት ወደ ጌታ እምነትና ወደ ንስሃው ወደሚመሩት የነቢያት ቅዱስ ትንቢቶችም የተመሩት ሁሉ—

ስለዚህ፣ ይህንን እንደሚያውቁ የመጡ ሁሉ፣ በእምነታቸውና ነፃ በተደረጉበትም ነገር ፅኑ እናም የማይነቃነቁ መሆናቸውን በእራሳችሁ አውቃችኋል።

እናም ደግሞ የጦር መሳሪያዎቻቸውን እንደቀበሩና፣ በሆነ አጋጣሚ ኃጢያትን እንሰራለን ብለው በመፍራታቸውም መሣሪያዎቻቸውን ለማንሳት እንደሚፈሩ ታውቃላችሁ፤ አዎን፣ ኃጢያትን ለመስራት መፍራታቸውን ለመመልከት ትችላላችሁ—እነሆም፣ በጠላቶቻቸው እንዲረገጡና እንዲገደሉ ይፈቅዳሉ፣ ጎራዴዎቻቸውንም በእነርሱ ላይ አያነሱም፣ እናም ይህ የሆነበት በክርስቶስ ባላቸው እምነት ነው።

እናም እንግዲህ፣ በሚያምኑበት በዚያ ነገር ሲያምኑ፣ የማያወላውሉ በመሆናቸው፣ ምክንያቱም አንዴ በተገለፀላቸው ጊዜ ፅኑ በመሆናቸውም፣ እነሆ ጌታ ይባርካቸዋል፣ እናም ኃጢአተኞች ቢሆኑም ዘመናቸውን ያረዝምላቸዋል—

፲፩ አዎን፣ እምነት አጥተው ቢመነምኑም፣ በአባቶቻችን እንዲሁም ደግሞ በነቢዩ ዜኖስ፣ እንዲሁም በሌሎች ብዙ ነቢያት ወንድሞቻችን ላማናውያን ድጋሚ እውነትን ወደማወቅ መመለስን በተመለከተ የተናገሩበት ቀን እስከሚመጣ ድረስ ጊዜ ቀኖቻቸውን ጌታ ያረዝመዋል

፲፪ አዎን፣ እንዲህ እላችኋለሁ፣ በኋለኞቹ ጊዜያት የጌታ ቃል ኪዳን ለወንድሞቻችን ለላማናውያንም ይቀርባል፤ እናም ብዙ ስቃዮችም የሚመጡባቸው ቢሆንምና፣ በምድር ገፅ ላይም ለመጠለያቸው ሥፍራን ሳያገኙ ወዲህና ወዲያ ቢሰደዱም፣ ቢታደኑም፣ ቢመቱም፣ እናም ከሀገር ውጪ ቢባረሩም፤ ጌታ ለእነርሱ መሃሪ ይሆናል።

፲፫ እናም ይህም የሚሆነው ታላቁና እውነተኛው እረኛ ወደሆነው ወደ አዳኛቸው እውቀት ወደሆነው እውነታዊ እውቀት እንደሚመጡ፣ እናም ከእርሱ በጎችም ጋር አብረው እንደሚቆጠሩ በተተነበየው መሰረት ነው።

፲፬ ስለዚህ እንዲህ እላችኋለሁ፣ ንስሃ ካልገባችሁ ከእናንተ ይልቅ ለእነርሱ የተሻለ ይሆናል።

፲፭ እነሆም፣ ለእናንተ የታዩት ኃያል ስራዎች ለእነርሱ፣ አዎን፣ በአባቶቻቸው ወግ አማካይነት እምነት አጥተው ለመነመኑት፣ የታዩ ቢሆን ኖሮ በድጋሚ እምነት በማጣት እንደማይመነምኑ እራሳችሁ ለመመልከት ትችላላችሁ።

፲፮ ስለዚህ፣ ጌታ እንዲህ አለ፥ ፈፅሞ አላጠፋቸውም፣ ነገር ግን በጥበብ ቀኔ ወደ እኔ እንዲመለሱ አደርጋቸዋለሁ፣ ይላል ጌታ።

፲፯ እናም እንግዲህ እነሆ፣ ጌታ ስለኔፋውያን እንዲህ ይላል፥ ንስሃ ካልገቡና፣ እንደፈቃዴም ካላደረጉ፣ ምንም እንኳን ብዙ አስደናቂ ስራዎች በመካከላቸው ብሰራም እምነት ስለሌላቸው ፈፅሞ አጠፋቸዋለሁ፣ ይላል ጌታ፤ እናም በእውነት ጌታ ህያው እንደሆነ እነዚህም ነገሮች ይሆናሉ ይላል ጌታ።