ቅዱሳት መጻህፍት
አልማ ፷


ምዕራፍ ፷

ሞሮኒ መንግስቱ ሠራዊቱን ችላ ማለቱን በተመለከተ ለፓሆራን ወቀሳ አቀረበ—ጌታ ፃድቃኖች እንዲገደሉ ይፈቅዳል—ኔፋውያን ከጠላቶቻቸው እራሳቸውን ለማስለቀቅ ያላቸውን ኃይል እንዲሁም ዘዴዎች በሙሉ መጠቀም ይኖርባቸዋል—ሞሮኒ ለሠራዊቱ እርዳታ ካልተደረገ ከመንግስት ጋር እንደሚዋጋ አስጠነቀቀ። በ፷፪ ም.ዓ. ገደማ።

እናም እንዲህ ሆነ ሞሮኒ ለሀገሪቱ አስተዳዳሪ፣ ለፓሆራን በድጋሚ ፃፈና፣ የፃፈውም ቃል እንዲህ ይል ነበር፥ እነሆ፣ በዛራሔምላ ከተማ ዋና ዳኛና፣ በምድሪቱ አስተዳዳሪ ለሆነው ለፓሆራን፣ እናም ደግሞ የጦር ጉዳያቸውን በተመለከተ እንዲያስተዳድሩና እንዲመሩ ከእነዚህ ሁሉ መካከል በህዝብ ለተመረጡት፣ ደብዳቤዬን አቀርባለሁ።

እነሆም፣ በወቀሳ መልክ ለእነርሱ በመጠኑ የምለው አለኝ፤ እነሆም፣ እናንተ ራሳችሁም ሰዎችን በአንድ ላይ እንድትሰበስቡና፣ በጎራዴና፣ በሻምላ፣ እንዲሁም በሁሉም ዓይነት የጦር መሳሪያዎች እንድታስታጥቁ እናም ላማናውያን ወደ ምድራችን በመጡበት በየትኛውም አቅጣጫ እንድትልኩአቸው ተሹማችኋል።

እናም እንግዲህ እነሆ፣ እኔ ራሴና፣ ደግሞ የእኔ ሰዎችና፣ ደግሞ ሔለማን፣ እና የእርሱ ሰዎች ታላቅ የሆነን ስቃይ ተሰቃይተናል፤ አዎን፣ በረሃብ፣ በጥማትና፣ በድካም፣ እናም በሁሉም ዓይነት ስቃይ ተሰቃይተናል።

ነገር ግን እነሆ፣ የተሰቃየነው ይህ ሁሉ ቢሆን ኖሮ፣ አናጉረመርምም እንዲሁም ወቀሳ አናቀርብም ነበር።

ነገር ግን እነሆ፣ በህዝባችን መካከል ግድያው ከፍተኛ ነበር፣ አዎን፣ በሺህ የሚቆጠሩ በጎራዴው ወድቀዋል፣ ለወታደሮቻችን በቂ ብርታትንና እርዳታን ብታደርጉ ኖሮ፣ ውጤቱም ሌላ በሆነ ነበር። አዎን በእኛም ላይ ችላ ባይነታችሁ ታላቅ ነበር።

እናም እንግዲህ እነሆ፣ የዚህ እጅግ ታላቅ የሆነ ችላ ባይነት መንስኤን ማወቅ እንፈልጋለን፤ አዎን፣ ለሀሳብ የለሽነትታችሁ ምክንያትን ማወቅ እንፈልጋለን።

ጠላቶቻችሁ በዙሪያችሁ የሞትን ስራ በሚያስራጩበት ወቅት በዙፋናችሁም ምንም ሳታስቡ ለመቀመጥ እንችላለን ብላችሁ ታስባላችሁን? አዎን፣ በሺህ የሚቆጠሩ ወንድሞቻችሁን ሲገድሉባችሁ—

አዎን፣ ለእርዳታ ወደእናንተ የሚመለከቱትንም፤ አዎን በእናንተም እንዲደገፉ በምትገኙበት ቦታ ያስቀምጡአችሁ ሲገድሉባችሁ፣ አዎን፣ ወታደሮችን እንዲያበረቱአቸው ወደእነርሱ ለመላክ፣ እናም ብዙ ሺህ የሚሆኑትን በጎራዴ ከመቆረጥ ባዳናችሁ ነበር።

ነገር ግን እነሆ፣ ይህ ብቻም አይደለም—ብዙዎች ለዚህ ህዝብ ደህንነት ታላቅ ፍላጎት ስለነበራቸው እስከሚዋጉ፣ እናም ደማቸው ፈሶም እስከሚሞቱ ድረስ ስንቃችሁን ያዛችሁባቸው፤ አዎን፣ እናም ለእነርሱ እጅግ ታላቅ የሆነ ግዴለሽነት ስለነበራችሁ ይህንን ያደረጉት በረሃብ ሊጠፉ ሲቃረቡ ነበር።

እናም እንግዲህ፣ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ—የምትወደዱ መሆን ነበረባችሁ፤ አዎን፣ እናም ለዚህ ህዝብ ደህንነትና፣ ነፃነት ይበልጥ በትጋት ራሳችሁን ማነሳሳት ነበረባችሁ፤ ነገር ግን እነሆ በሺህ የሚቆጠሩት ሰዎች ደም ለበቀል በራሳችሁ ላይ እስከሚመጣ ድረስ ችላ አላችኋቸው፤ አዎን፣ ጩኸታቸው፣ እናም ስቃያቸው ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ የታወቀ ነው—

፲፩ እነሆ፣ እናም በታላቁ የእግዚአብሔር ቸርነት ምክንያት ምንም ነገር ሳትፈፅሙ ያድነናል፣ እርሱም ትቶአችሁ በዙፋናችሁ ላይ መቀመጥ እንችላለን ብላችሁ ትገምታላችሁን? እነሆ፣ ይህንን የምትገምቱ ከሆነ ግምታችሁ ከንቱ ነው።

፲፪ ብዙዎች ወንድሞቻችሁ ስለሞቱ በኃጢአታቸው ነው የተገደሉት ብላችሁ ትገምታላችሁን? እኔ እላችኋለሁ፣ እንደዚህ የምትገምቱ ከሆነ ግምታችሁ ከንቱ ነው፤ እንዲህ እላችኋለሁና፣ ብዙዎች በጎራዴ ሞተዋል፤ እናም እነሆ ይህ ኩነኔያችሁ ነው፤

፲፫ ጌታ ትክክለኛው ፍርዱና ቅጣቱ በኃጢአተኞች ላይ ይሆን ዘንድ ፃድቃኖች እንዲገደሉ ይፈቅዳል፤ ስለዚህ ፃድቃኖች ስለተገደሉ የጠፉ ናቸው ብላችሁ አትገምቱ፤ ነገር ግን እነሆ በጌታ በአምላካቸው ዘንድ ያርፋሉ።

፲፬ እናም አሁን እነሆ፣ እላችኋለሁ እጅግ ሰነፎች በመሆናቸው፤ አዎን፣ በመንግስታችንም ስንፍና ቢሆን፣ እናም ለወንድሞቻቸውም፣ አዎን፣ ለተገደሉትም ቢሆን ባላቸው ታላቅ ችላ ባይነት፣ የእግዚአብሔር ቅጣት በእነዚህ ሰዎች ላይ እንዳይሆን በጣም እፈራለሁ።

፲፭ በአመራራችን በተጀመረው ኃጢያት ባይሆን ኖሮ ጠላቶቻችን በእኛ ላይ ኃይልን እንዳያገኙ ለመቋቋም ይቻለን ነበር።

፲፮ አዎን፣ በራሳችን መካከል በተጀመረው ጦርነት ባይሆን ኖሮ፤ አዎን፣ በራሳችን መካከል ብዙ ደም መፋሰስ እንዲሆን ባደረጉት በንጉሡ ሰዎች ባይሆን ኖሮ፤ አዎን፣ በመካከላችን ፀብ በነበረበት ጊዜ፣ ቀደም ሲል እንዳደረግነው እራሳችንን በአንድ ላይ ብናደርግ ኖሮ፤ አዎን፣ የንጉስ ሰዎች በእኛ ላይ እንደፈለጉት ኃይልና ስልጣን ባይሆን ኖሮ፤ በመካከላችን ለብዙ ደም መፋሰስ ምክንያት የሆነውን ጎራዴአቸውን ከማንሳት ይልቅ፣ ለነፃነታችን ምክንያት እውነተኞች ቢሆኑ፣ እናም ከእኛ ጋር ተቀላቅለው በጠላቶቻችን ላይ ቢሄዱ፣ አዎን፣ በጌታ ብርታት ወደ እነርሱ ብንሄድ ጠላቶቻችንን እንበታትናቸው ነበር፣ ምክንያቱም ይህ የሚሆነው የጌታ ቃሉ ይፈፀም ዘንድ ነው።

፲፯ ነገር ግን እነሆ፣ ላማናውያን ምድራችንን ለመውሰድ መጥተዋል፣ እናም ህዝባችንን በጎራዴ እየገደሉ፤ አዎን፣ ሴቶቻችንንና፣ ልጆቻችንን፣ እናም ደግሞ ምርኮኞች አድርገው እየወሰዱአቸው ናቸው፣ ሁሉንም ዓይነት ስቃይ እንዲሰቃዩ እያደረጉአቸው ናቸው፤ ይህም ኃይልና ሥልጣን በሚሹ ታላቅ ኃጢያት፣ አዎን፣ እንዲሁም በእነዚያ የንጉስ ሰዎች ምክንያት ነው።

፲፰ ነገር ግን ይህንን በተመለከተ ለምን ብዙ እላለሁኝ? እራሳችሁም ብትሆኑ ስልጣንን የምትፈልጉ መሆናችሁን አናውቅም። እናንተ ለሀገራችሁ ከሀዲ እንደሆናችሁም አናውቅም።

፲፱ ወይም ችላ ያላችሁን፣ ምግብም እንዳይላክልን እናም ደግሞ ወታደሮቻችን እንዲጠናከሩ ሰዎች እንዳይላኩ ያደረጋችሁበት ምክንያት በሀገራችን ዋና ስፍራ በመሆናችሁ፣ እናም በጠባቂዎች በመከበባችሁ ነውን?

የጌታ የአምላካችሁን ትዕዛዛት ረስታችኋልን? አዎን አባቶቻችን በምርኮ እንደነበሩስ ረስታችኋልን? ከጠላቶቻችን እጅ ብዙ ጊዜ መለቀቃችንን ረሳችሁትን?

፳፩ ወይም በዙፋናችን እንደተቀመጥን እና ጌታ የሰጠንን ዘዴዎች ሳንጠቀምባቸው ያድነናል ብላችሁ ትገምታላችሁን?

፳፪ አዎን፣ በሺዎች እንዲሁም በአስር ሺዎች ያለስራ በተቀመጡት ተከብባችሁ፤ በዙሪያችሁ በምድሪቱ ዳርቻ በሺህ የሚቆጠሩት በጎራዴ በተገደሉ ጊዜ፤ አዎን፣ በቆሰሉና በደሙ ጊዜ ያለስራ ትቀመጣላችሁን?

፳፫ አሁንም ተቀምጣችሁ እነዚህን ነገሮች በምትመለከቱበት ጊዜ እግዚአብሔር እንከን የሌላችሁ አድርጎ ይቆጥረናል ብላችሁ ትገምታላችሁን? እነሆ እኔ ግን እንደዚህ አድርጎ አይቆጥራችሁም እላለሁ። እንግዲህ የመያዣው እቃ ውስጥ በመጀመሪያ እንዲጠራ፣ እናም ደግሞ የእቃው ውጭ እንዲጠራ እግዚአብሔር መናገሩን እንዲያስተውሉ እፈልጋለሁ።

፳፬ እናም እንግዲህ፣ ለሰራችሁት ስራ ንስሃ ካልገባችሁና፣ በስራችሁ ንቁ ካልሆናችሁ፣ እንዲሁም በድጋሚ ያገኛትን የሀገራችንን ክፍል ይደግፉት ዘንድና፣ ምናልባት ደግሞ በዚህኛው ክፍል የተቀረውን ንብረታችንን እናገኝ ዘንድ፣ እናም ወደ እኛምና፣ ደግሞ ለሔለማን፣ ምግብና ሰው ካልላካችሁ፤ እነሆ የውስጥ መያዣችንን እቃ፣ አዎን የመንግስታችን የበላይ ሹማምንቶችንም ቢሆን፣ እስከምናጠራ ከላማናውያን ጋር መጣላቱ አስፈላጊ አይደለም።

፳፭ እናም የደብዳቤዬን መልስ ካልሰጠኸኝ በቀር፣ እናም ወጥተህና እውነተኛውን የነፃነት መንፈስ ካላሳየኸኝና፣ ወታደሮቻችንን ካላበረታህና ካላጠናከርህና፣ ለድጋፋቸው ምግብ ካልሰጠኻቸው እነሆ የነፃነት ሰዎቼን ይህንን ክፍል እንዲያስተዳድሩ እተዋቸዋለሁ፤ እናም ሌላ ኃይል በእነርሱ ላይ መስራት እንዳይችል የእግዚአብሔርን ብርታትና በረከት በእነርሱ ላይ አደርጋለሁ—

፳፮ እናም ይህን የማደርገው በታላቁ እምነታቸው፣ እናም በመከራቸው ጊዜ በነበራቸው ትዕግስት ነው—

፳፯ እናም ወደ እናንተ እመጣለሁና፣ በመካከላችሁ ነፃነት የሚፈልግ ቢኖር፣ አዎን፣ የቀረም የነፃነት ብልጭታ ቢኖር፣ እነሆ፣ ኃይልና ስልጣንን ያለአግባብ በመካከላችሁ የሚያነሳሱት እንኳን እስከሚጠፉ ድረስ አመፅ አስነሳለሁ።

፳፰ አዎን፣ እነሆ ኃይላችሁንም ሆነ ስልጣናችሁን አልፈራም፤ ነገር ግን አምላኬን ነው የምፈራው፤ እናም እንደትዕዛዛቱ ሀገሬን ለመከላከል ጎራዴዬን አነሳለሁ፤ እናም በክፋታችሁ የተነሳ ነው ብዙዎች የጠፋት።

፳፱ እነሆ ይህ ጊዜው ነው፤ አዎን አሁን ጊዜው ደርሷል፣ ራሳችሁን፣ ሀገራችሁንና፣ ልጆቻችሁን ለመከላከል ካላነሳሳችሁ የፍትህ ጎራዴ በእናንተ ላይ ይንዠባለላል፤ አዎን፣ እናም በእናንተ ላይ ይሆናል፣ እንዲሁም ፈፅሞም ለጥፋታችሁ ይሆናል።

እነሆ፣ ከእናንተ እርዳታን እጠብቃለሁ፤ እናም፣ እርዳታችንን እንድናገኝ ካልሰራችሁ በቀር፣ እነሆ፣ ወደ ዛራሔምላ ምድርም እንኳን እመጣለሁና፣ ለነፃነታችን መንስኤ የዚህን ህዝብ እድገት ለማገድ ስልጣን ከዚህ ወዲያ ሊኖርህ እስከማይችል ድረስ በጎራዴ እመታሃለሁ።

፴፩ እነሆም፣ ጌታ እንድትኖር፣ እናም ፃድቅ ህዝቡን ለማጥፋት በክፋትህ እንድትጠነክር አይፈቅድልህም።

፴፪ እነሆ ክፋትህ ክብርህን እና የዓለምን ከንቱ ነገሮች ለመውደድ ሆኖ እያለ፣ ጌታ በአባቶቻቸው ወግ ምክንያት ጥላቻ ያላቸውን፣ አዎን እናም ይኸውም ከእኛ በተገነጠሉት ላይ በተጨመረባቸው ላማናውያን ላይ ጌታ በፍርድ እንደሚመጣባቸውና፣ ራሳችሁን ያድናችኋል ብላችሁ ትገምታላችሁን?

፴፫ የእግዚአብሔርን ህግጋት መተላለፍህን ታውቃለህ፣ እናም እነዚህን በእግርህ መርገጥህንም ታውቃለህ። እነሆ ጌታ እንዲህ ብሎኛል፥ ገዢ አድርገህ የሾምካቸው ለኃጢአታቸው እና ለክፋታቸው ንስሃ ካልገቡ ከእነርሱ ጋር ሄደህ መዋጋት ይኖርብሃል።

፴፬ እናም እንግዲህ እነሆ፣ እኔ፣ ሞሮኒ፣ የአምላኬን ትዕዛዛት ለመጠበቅ በገባሁት ቃል ኪዳን መሰረት እገፋፋለሁ፤ ስለዚህ የእግዚአብሔርን ቃል እንድትቀበሉ እፈልጋለሁ፣ እናም ከቀለባችሁና፣ ከሰዎቻችሁ ላኩልኝ፣ እናም ደግሞ ለሔለማን በፍጥነት ላኩለት።

፴፭ እናም እነሆ ይህንን የማታደርጉ ከሆነ በፍጥነት ወደ እናንተ እመጣለሁ፤ እነሆም፣ እግዚአብሔር በረሃብ እንድንጠፋ አይፈቅድም፤ ስለዚህ በጎራዴም ቢሆን ከምግባችሁ ይሰጠናል። እንግዲህ የእግዚአብሔርን ቃል ፈፅሙ።

፴፮ እነሆ፣ እኔ ሊቀ ሻምባል ሞሮኒ ነኝ። ፍላጎቴ ለስልጣን ሳይሆን፣ ነገር ግን ይህን ጎትቶ ለማውረድ ነው። የዓለምን ክብር ሳይሆን፣ የአምላኬ ክብርን እናም የሀገሬን ነፃነትና ደህንነት ነው የምፈልገው። እናም ደብዳቤዬን አበቃለሁ።