ቅዱሳት መጻህፍት
አልማ ፵፫


ምዕራፍ ፵፫

አልማ እና ልጆቹ ቃሉን ሰበኩ—ዞራማውያን እና ሌሎች ተቃዋሚ ኔፋውያን ላማናውያን ሆኑ—ላማናውያን በኔፋዉያን ላይ ለጦርነት መጡባቸው—ሞሮኒ ኔፋውያንን በሚከላከል ጥሩር አስታጠቃቸው—ጌታ ለአልማ የላማናውያንን የጦር ስልት አሳየው—ኔፋውያን፣ ቤቶቻቸውን፣ ነፃነታቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን እና ኃይማኖታቸውን ተከላከሉ—የሞሮኒ እና የሌሂ ሠራዊት ላማናውያንን ከበቡአቸው። በ፸፬ ም.ዓ. ገደማ።

እናም አሁን እንዲህ ሆነ የአልማ ልጆች ቃሉን ለማወጅ በህዝቡ መካከል ሄዱ። እናም አልማ፣ እራሱ ደግሞ ማረፍ አልቻለምና፣ ደግሞ ወደፊት ተጓዘ።

አሁን በትንቢቱ መንፈስና ራዕይ አማካኝነት ቃሉንና እውነትን ከመስበካቸው ውጪ ስለስብከታቸው ከዚህ የበለጠ ምንም የምንለው አይኖርም፤ እናም በተጠሩበት በቅዱሱ የእግዚአብሔር ሥርዓት መሠረት ሰበኩ።

እናም አሁን በመሳፍንቱ አገዛዝ በአስራ ስምንተኛው የንግስ ዘመን በኔፋውያንና በላማናውያን መካከል ስለነበረው የጦርነት ታሪክ እመለሳለሁ።

እነሆም፣ እንዲህ ሆነ ዞራማውያን ላማናውያን ሆኑ፤ ስለዚህ፣ በአስራ ስምንተኛው ዓመት መጀመሪያ ላይ የኔፋውያን ሕዝቦች ላማናውያን በእነርሱ ላይ ሲመጡ ተመለከቱ፤ ስለዚህ ለጦርነት ተዘጋጁ፤ አዎን፣ ወታደሮቻቸውንም በኢየርሾን ምድር በአንድ ላይ ሰበሰቡ።

እናም እንዲህ ሆነ ላማናውያን ከሺህ ወታደሮቻቸው ጋር መጡ፤ እናም የዞራማውያን ምድር ወደሆነችው ወደ አንቲዮኑም ምድር መጡ፤ እናም ዜራሔምና ተብሎ የሚጠራው ሰውም መሪያቸው ነበር።

እናም አሁን፣ አማሌቂውያን ከላማናውያን የበለጡ ኃጢአተኞችና የገዳይ ፀባይ ያላቸው በመሆናቸው፣ ስለዚህ፣ ዛራሄምናህ በላማናውያን ላይ ዋና ሻምበልን ሾመ፣ እናም ሻምበሎቹ በሙሉ አማሌቂውያንና ዞራማውያን ነበሩ።

አሁን እርሱ ይህንን ያደረገው በኔፋውያን ላይ ያላቸውን ጥላቻ ይጠብቁት ዘንድ፣ እነርሱም የእርሱን ዕቅድ ይፈፅሙ ዘንድ በቁጥጥሩ ስራ ያደርጋቸው ዘንድ ነው።

እነሆም፣ የእርሱ ዓላማ ላማናውያን በኔፋውያን ላይ በቁጣ እንዲነሳሱ ነበር፤ ይህንም ያደረገው በእነርሱም ላይ ታላቅ ኃይልን በግድ ይወስድ ዘንድ፣ እናም ደግሞ ኔፋውያንን በምርኮ ስር በማምጣት በእነርሱ ላይ ኃይል ያገኝ ዘንድ ነው።

እናም አሁን የኔፋውያን ዓላማ ከጠላቶቻቸው እጅ ይጠብቋቸው ዘንድ ምድራቸውንና፣ ቤታቸውን፣ እንዲሁም ሚስቶቻቸውንና፣ ልጆቻቸውን ለመደገፍ ነበር፣ እናም ደግሞ እግዚአብሔርን እንደ ፍላጎቶቻቸው ያመልኩ ዘንድ፣ ልዩ መብቶቻቸውንና ጥቅሞቻቸውን፣ አዎን፣ እናም ደግሞ ነፃነታቸውን ይጠብቁ ዘንድ ነበር።

በላማናውያን እጅ ቢወድቁ፣ ላማናውያን እውነተኛና ህያው የሆነውን አምላክ እግዚአብሔርን በእውነትና በመንፈስ የሚያመልከው ማንኛውም እንደሚያጠፉ ያውቃሉና።

፲፩ አዎን፣ እናም ደግሞ የአሞን ህዝብ ተብለው በሚጠሩት ወንድሞቻቸው በአንቲ-ኔፊ-ሌሂዎችን ህዝብ ላይ ላማናውያን የከፋ ጥላቻ እንዳላቸው ያውቃሉ—እናም እነርሱ የጦር መሳሪያን አያነሱም፣ አዎን፣ ቃል ኪዳንን ገብተዋል እና ይህንንም አያፈርሱም—ስለዚህ፣ እነርሱ በላማናውያን እጅ ከወደቁ ይጠፋሉ።

፲፪ እናም ኔፋውያን እነርሱ እንዲጠፉ አልፈለጉም፤ ስለዚህ የውርስ ምድርንም ሰጡአቸው።

፲፫ እናም የአሞን ህዝብ ለኔፊ ህዝብ ወታደሮቻቸውን ለመርዳት ካሉአቸው ነገር አብዛኛውን ሰጡአቸው፤ እናም ኔፋውያን ብቻ የላማንና ልሙኤል ዝርያ ቅንጅት የሆኑትን ላማናውያንና፣ የእስማኤል ልጆች የሆኑትን፣ እንዲሁም አማሌቂውያንና ዞራማውያን ከነበሩትና፣ እም ከኔፋውያን የተገነጠሉት በሙሉ፣ እናም ከኖህ ካህናት ዝርያ የሆኑትን እንዲቋቋሙ ተገደዱ።

፲፬ እንግዲህ የእነርሱ ዝርያዎችም ቁጥራቸው እንደኔፋውያን የበዛ ነበር፤ እናም ኔፋውያን ደም እስከማፍሰስ ድረስ ከወንድሞቻቸው ጋር እንዲጣሉ እንዲህ ይገደዱ ነበር።

፲፭ እናም እንዲህ ሆነ የላማናውያን ወታደሮች በአንቲዮኑም ምድር በአንድ ላይ እንደተሰበሰቡ፣ እነሆ፣ የኔፋውያን ሠራዊትም በኢየርሾን ምድር እነርሱን ለመገናኘት ተዘጋጅተው ነበር።

፲፮ እንግዲህ፣ የኔፋውያን መሪ፣ ወይንም በኔፋውያን ላይ ዋና ሻምበል በመሆን የተሾመው—ዋናው አዛዥ የኔፋውያንን ሠራዊት በሙሉ የሚያዛቸው—እናም ስሙ ሞሮኒ ነበር፤

፲፯ እናም ሞሮኒ በኔፋውያን ወታደሮች ላይ ሙሉ በሙሉ አዛዥና የጦርነቱ አመራር ሰጪ ሆነ። እናም እርሱ በኔፊ ወታደሮች ላይ ዋና ሻምበል ሆኖ በተሾመበት ጊዜ ሀያ አምስት ዓመቱ ነበር።

፲፰ እናም እንዲህ ሆነ በኢየርሾን ዳርቻ ከላማናውያን ጋር ተገናኘ፤ እናም ህዝቡ በጎራዴና፣ በሻሙላና በሁሉም ዓይነት የጦር መሳሪያዎች ታጠቁ።

፲፱ እናም የላማናውያን ወታደሮች የኔፊን ህዝብ ወይንም፣ ሞሮኒ ህዝቡን በደረት ኪስና በእጅ የሚያዝ ጋሻ እንዳዘጋጃቸው በተመለከቱ ጊዜ፤ አዎን፣ እናም ደግሞ እራሳቸውን ለመከላከል ጋሻና ደግሞ ወፍራም ልብስ ለብሰው ነበር—

እንግዲህ የዜራሔምና ሠራዊት በእንደዚህ ዓይነት ነገር አልተዘጋጁም ነበር፤ እነርሱ ጎራዴ እናም ሻምላቸው፣ ቀስትና ወስፈንጥሮቻቸውና፣ ድንጋይና ወንጭፎቻቸው ብቻ ነበሩአቸው፤ በወገባቸው ላይ ከታጠቁት ቆዳ በስተቀር እርቃናቸውን ነበሩ፤ አዎን ከዞራማውያንና ከአማሌቂውያን በስተቀር ሁሉም እርቃናቸውን ነበሩ፤

፳፩ ነገር ግን በደረት ኪስም ሆነ በጋሻ አልታጠቁም ነበር—ስለዚህ፣ ምንም እንኳን ብዛታቸው ከኔፋውያን የበለጠ ቢሆንም ኔፋውያን ባሉአቸው የጦር መሳሪያዎች የተነሳ እጅግ ፈርተዋቸው ነበር።

፳፪ እነሆ፣ እንግዲህ እንዲህ ሆነ በኢየርሾን ዳርቻ በኔፋውያን ላይ ለመዋጋት አልደፈሩም፤ ስለዚህ ከአንቲዮኑም ምድር ወደ ምድረበዳው ሸሹ፣ እናም ወደ ማንቲ ምድር ይመጡና ምድሪቱንም ይወስዱ ዘንድ በሲዶም ወንዝ በኩል በምድረበዳው ጉዞአቸውን አደረጉ፤ ምክንያቱም የሞሮኒ ወታደሮች ወዴት እንደሚሄዱ ያውቃሉ ብለው አልገመቱም ነበር።

፳፫ ነገር ግን እንዲህ ሆነ፣ ወደ ምድረበዳው ወዲያው እንደሄዱ ሞሮኒ የጦር ሰፈራቸውን እንዲመለከቱ በምድረበዳው ሰላዮችን ላከ፤ እናም ሞሮኒ ደግሞ የአልማን ትንቢት በማወቁ፣ የኔፋውያን ወታደሮች እራሳቸውን ከላማናውያን ለመከላከል ወዴት መሄድ እንዳለባቸው ጌታን ለመጠየቅ በመፈለጉ ወደ አልማ ሰዎችን ላከ።

፳፬ እናም እንዲህ ሆነ የጌታ ቃል ወደ አልማ መጣና፣ ደካማ በሆነው ክፍል ህዝብን ለማጥቃት ይጀምሩ ዘንድ የላማናውያን ሠራዊት ወደ ማንቲ ምድር ለመምጣት በምድረበዳው በኩል እየተመሙ እንዳለ ለሞሮኒ መልዕክተኞች አልማ አስታወቀ። እናም መልዕክተኞቹ ሄዱና፣ መልዕክቱን ለሞሮኒ ተናገሩ።

፳፭ እንግዲህ ሞሮኒ፣ በማንኛውም መንገድ ላማናውያን መጥተው ከተማውን እንዳይወስዱ ዘንድ፣ ከወታደሮቹ የተወሰኑትን በኢየርሾን ምድር በመተው የቀሩትን ወታደሮቹን ወሰደ እናም ወደ ማንቲ ምድር ሄደ።

፳፮ እናም ሞሮኒ በዚያ ስፍራ ያሉት ሰዎች በሙሉ ምድራቸውንና ሀገራቸውን፣ መብታቸውን፣ እና ነፃነታቸውን ለመጠበቅ ከላማናውያን ጋር እንዲዋጉ በአንድ ላይ እንዲሰባሰቡ አደረገ፤ ስለዚህ ላማናውያን ለሚመጡበት ጊዜም ተዘጋጅተው ነበር።

፳፯ እናም እንዲህ ሆነ ሞሮኒ በምድረበዳው በሲዶም ወንዝ በስተምዕራብ በኩል በነበረው በሲዶም ወንዝ ዳርቻ አጠገብ ባለው ሸለቆ ወታደሮቹ እንዲደበቁ አደረገ።

፳፰ እናም ሞሮኒ የላማናውያን ወታደሮች የሚመጡበትን ጊዜ ያውቅ ዘንድ በዙሪያው ሰላዮችን አስቀመጠ።

፳፱ እናም እንግዲህ፣ ሞሮኒ የላማናውያንን ፍላጎት ስለሚያውቅ፣ ስለዚህ በምድሪቱም ላይ ለራሳቸው መንግስትን ያቋቁሙ ዘንድ ወንድሞቻቸውን ማጥፋት እናም በባርነት ስር ማድረግ ፍላጎታቸው ነበር፤

እናም ደግሞ ምድራቸው፣ ነፃነታቸውን እና ቤተክርስቲያናቸውን መጠበቅ የኔፋውያን ፍላጎት ብቻ መሆኑን በማወቁ፣ ስለዚህ በስልት እነርሱን መከላከል ኃጢያት አይደለም በማለት አሰበ፤ ስለዚህ፣ በሰላዮቹ አማካኝነት ላማናውያን የትኛውን መንገድ እንደሚወስዱ አወቀ።

፴፩ ስለዚህ፣ ሞሮኒ ወታደሮቹን ከፈለ፣ እናም ግማሹን ወደ ሸለቆው ወሰደና፣ በስተምስራቅ፣ እናም በሪፕላ ኮረብታ በስተደቡብ ሸሸጋቸው፤

፴፪ እናም የቀሩትን በሲዶም ወንዝ በስተምዕራብ በኩል፣ እናም በማንቲ ምድር በታችኛው ዳርቻ በኩል ደበቃቸው።

፴፫ እናም እንደፍላጎቱ ወታደሮቹን ካስቀመጠ በኋላ፣ ላማናውያንን ለመገናኘት ተዘጋጅቶ ነበር።

፴፬ እናም እንዲህ ሆነ ላማናውያን ግማሾቹ የሞሮኒ ወታደሮች በተደበቁበት ስፍራ በኮረብታው በስተሰሜን በኩል መጡ።

፴፭ እናም ላማናውያን ሪፕላ ኮረብታን ሲያልፉና፣ ወደ ሸለቆው ሲመጡ፣ እናም የሲዶምን ወንዝ መሻገር እንደጀመሩ፣ ሌሂ በተባለው ሰው የተመሩት በስተደቡብ በኮረብታው የተሸሸጉት ወታደሮች ወደፊት መጓዝ ጀመሩ፤ እናም በስተምስራቅ ላማናውያንን ከበስተኋላቸው እንዲከቡአቸው አደረገ።

፴፮ እናም እንዲህ ሆነ ላማናውያን ኔፋውያን ከበስተኋላቸው እንደመጡባቸው በተመለከቱ ጊዜ፣ ወደ እነርሱ ተመለሱ፣ እናም ከሌሂ ሠራዊት ጋር መዋጋት ጀመሩ።

፴፯ እናም ሞትም በሁለቱም ወገን ተጀመረ፣ ነገር ግን በላማናውያን በኩል ይበልጡን አሰቃቂ ነበር፣ ምክንያቱም እርቃናቸው በእያንዳንዱ ምት የሞት ስራን በሚያመጡት በኔፋውያን ጎራዴ እናም ሻሙላ ከባድ ምት ተጋልጦ ነበር።

፴፰ በሌላ መልኩ፣ ኔፋውያን በደረት ኪሳቸው፣ እናም በእጅ በሚያዙት ጋሻዎቻቸው፣ እናም በራስ ቆባቸው የሰውነታቸውን አስፈላጊ ቦታዎች በመከላከላቸው ወይም ከላማናውያን ምት የሰውነታቸውን አስፈላጊ ቦታዎች በመከላከላቸው፣ አንዳንዴ ከኔፋውያን መካከል በላማናውያን ጎራዴዎችና ደም በመፍሰስ ምክንያት የሚወድቁ ነበሩ።

፴፱ እናም እንዲህ ሆነ፣ ላማናውያን በመካከላቸው በነበረው ታላቅ ጥፋት የተነሳ ወደ ሲዶም ወንዝ እስከሚሸሹም ድረስ ፈሩ።

እና እነርሱም በሌሂና በሰዎች እየተሳደዱ ነበር፤ በሌሂም አማካኝነት ወደ ሲዶም ውኃ ተገፉና፣ የሲዶምን ውኃ ተሻገሩ። እናም ሌሂ እነርሱ የሲዶምን ወንዝ እንዳይሻገሩ ወታደሮቹን በወንዙ ዳርቻ እንዲቆዩ አደረገ።

፵፩ እናም እንዲህ ሆነ በሲዶም ወንዝ በሌላኛው በኩል ሞሮኒና ወታደሮቹ ላማናውያኖችን አገኙአቸው፣ እናም እነርሱን ማጥቃትና መግደል ጀመሩ።

፵፪ እናም ላማናውያን ከሞሮኒ ሠራዊት ፊት ወደማንቲ በድጋሚ ሸሹ፤ እናም በድጋሚ ከሞሮኒ ወታደሮች ጋር ተገናኙ።

፵፫ እንግዲህ በዚህ ሁኔታ ላማናውያን በኃይል ተዋጉ፤ አዎን ላማናውያን ከመጀመሪያው ጀምሮም እንኳን ቢሆን በታላቅ ብርታትና ድፍረት እንደዚህ ሲዋጉ በጭራሽ አይታወቅም ነበር።

፵፬ እናም ላማናውያን በዋና ሻምበሎቻቸውና መሪዎቻቸው በነበሩት በዞራማውያን እና አማሌቂውያን፣ እንዲሁም ዋና ሻለቃቸው በነበረውና፣ ዋና መሪና አዛዣቸው በሆነው ዛራሄምናህ ተቀስቅሰው ነበር፤ አዎን፣ እንደዘንዶ ተዋጉ፣ ብዙ ኔፋውያንም በእጃቸው ተገደሉ፤ አዎን፣ የራስ ቆባቸውን መትተው ሁለት ቦታ ከፈሉባቸው፣ እናም የደረት ኪሶቻቸውን በሱባቸው፣ ብዙዎችን እጆቻቸውንም ቆረጡባቸው፤ እናም ላማናውያኑ በኃያሉ ቁጣቸው እንደዚህ መቱአቸው።

፵፭ ይሁን እንጂ፣ ኔፋውያን የተነሳሱት በተሻለ ምክንያት ነበር፣ ምክንያቱም እነርሱ የሚዋጉት ለንግስናም ሆነ ለስልጣን ሳይሆን፣ ለሀገራቸውና ለነፃነታቸው፣ ለሚስቶቻቸውና ለልጆቻቸው እናም ላሉዋቸው ነገሮች ሁሉ፣ አዎን ለሚያመልኩበት ስርዓትና ለቤተክርስቲያናቸው ነበር።

፵፮ እናም ኔፋውያን ለአምላካቸው ይገባዋል ብለው የሚሰማቸውን ስራ ነበር የሰሩት፤ ምክንያቱም ጌታ ለእነርሱ እናም ደግሞ ለአባቶቻቸው እንዲህ ብሎአቸው ነበርና፥ ለመጀመሪያውም ሆነ ለሁለተኛው ጥፋት ተጠያቂዎች እስካልሆናችሁ ድረስ በጠላቶቻችሁ እጅ እንድትገደሉ አትፍቀዱ።

፵፯ እናም በድጋሚ ጌታ እንዲህ አለ፥ ቤተሰቦቻችሁን እስከደም ጠብታ መከላከል ትችላላችሁ። ስለዚህ ኔፋውያን እራሳቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውንና ምድራቸውን፣ እናም ሀገራቸውንና፣ መብታቸውንና ኃይማኖታቸውን ለመጠበቅ ከላማናውያን ጋር ተዋጉ።

፵፰ እናም እንዲህ ሆነ የሞሮኒ ሰዎች የላማናውያንን ኃያልነትና ቁጣ በተመለከቱ ጊዜ፣ በመፍራትና በመሸማቀቅ በፊታቸው ለመሸሽ ሊጀመሩ ነበር። እናም ሞሮኒ የእነርሱን ፍላጎት ተረዳና ቃሉን ወደ እነርሱ ላከና፣ በእንደዚህ ዓይነቱ ሀሳብ ልባቸውን፣ አዎን፣ የምድራቸውን፣ የነፃነታቸውን፣ አዎን፣ ከባርነት ነፃ የመውጣታቸውን ሀሳብንም ቀሰቀሰ።

፵፱ እናም እንዲህ ሆነ ላማናውያንን ተመልሰው አጠቁና፣ ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ለነፃነታቸውና ከባርነት እንዲለቀቁ በአንድ ድምፅ ጮሁ

እናም ላማናውያንን በኃይል መቋቋማቸውን ጀመሩ፤ እናም በዚሁ ሰዓት ለነፃነታቸው ወደ ጌታ ጮሁ፣ ላማናውያንም ከፊታቸው መሸሽ ጀመሩ፤ እናም ወደ ሲዶም ውኃም ሸሹ።

፶፩ እንግዲህ፣ ላማናውያን በቁጥር ብዙ ነበሩ፤ አዎን፣ ከኔፋውያን በቁጥር እጥፍ ያህል ነበሩ፤ ይሁን እንጂ በሲዶም ወንዝ ዳርቻ በሸለቆው በአንድነት እስኪሰባሰቡ ተሰደዱ።

፶፪ ስለዚህ የሞሮኒ ወታደሮች ላማናውያንን ከሞላ ጎደል ከበቡአቸው፤ አዎን፣ በወንዙ በሁለቱም በኩል፣ እነሆ፣ በስተምስራቅም የሌሂ ሰዎች ነበሩና።

፶፫ ስለዚህ ዜራሔምና የሌሂን ሰዎች በሲዶም ወንዝ በስተምስራቅ፣ እናም የሞሮኒን ወታደሮች በሲዶም ወንዝ በስተምዕራብ፣ በኔፋውያን መከበባቸውን በተመለከቱ ጊዜ በፍርሃት ተውጠው ነበር።

፶፬ እንግዲህ፣ ሞሮኒ ፍርሃታቸውን በተመለከተ ጊዜ የደም መፍሰሱ እንዲቆም ህዝቡን አዘዘ።