ቅዱሳት መጻህፍት
አልማ ፵፪


ምዕራፍ ፵፪

ሟችነት ሰዎችን ንስሃ እንዲገቡ እናም እግዚአብሔርን እንዲያገለግሉ የሚያስችል የሙከራ ጊዜ ነው—የአዳም መውደቅ በሰው ዘር ሁሉ ላይ ጊዜያዊ እናም መንፈሳዊ ሞትን አመጣ—ቤዛነት በንስሃ አማካይነት ይመጣል—እግዚአብሔር እራሱ ለዓለም ኃጢያት ክፍያን ይከፍላል—ንሰሃ የሚገቡ ምህረትን ያገኛሉ—ሌሎች በሙሉ በእግዚአብሔር ፍትህ ስር ናቸው—ምህረት በኃጢያት ክፍያው አማካኝነት ይመጣል—እውነተኛ ንስሃ ገቢዎች ብቻ ይድናሉ። በ፸፬ ም.ዓ. ገደማ።

እናም እንግዲህ ልጄ፣ ኃጢአተኞችን በመቅጣት የእግዚአብሔርን ፍትህ በተመለከተ፣ አንተ መረዳት የማትችለው አዕምሮህን የሚረብሽ ከዚህ የበለጠ በመጠኑ እንዳለ አስተውላለሁ፤ ኃጢአተኞች ወደ ሥቃይ መመደባቸው ፍትሃዊ አይደለም በማለት ገምተሃልና።

እንግዲህ እነሆ ልጄ ይህንን ነገር ለአንተ እገልፅልሃለሁ። እነሆም፣ ጌታ እግዚአብሔር የመጀመሪያ ቤተሰቦቻችንን ከተወሰዱበት ስፍራ መሬቱን እንዲያርሱ ከዔድን ገነት ካስወጣቸው በኋላ—አዎን፣ ሰውን አስወጣ፣ እናም ጌታ እግዚአብሔር በዔድን ገነት በስተምስራቅ ጫፍ፣ ኪሩቤልን፣ እናም የምትገለባበጥ የነበልባል ሰይፍን፣ የህይወት ዛፍን ለመጠበቅ አስቀመጠ—

እንግዲህ፣ ሰው መልካሙንና መጥፎውን በማወቅ እንደ አምላክ መሆኑን እናያለን፤ እናም እጁን በመዘርጋትና፣ ደግሞ ከህይወት ዛፍ በመውሰድ፣ እናም በመብላት ለዘለዓለም ለመኖር የሚችል እንዳይሆን፣ ፍሬውንም እንዳይካፈል፣ ጌታ እግዚአብሔር ኪሩቤልንና ነበልባል ሰይፉን አስቀመጠ—

እናም ለሰዎች የንስሃ ጊዜ እንደተሰጠም እንመለከታለን፤ አዎን፣ የሙከራ ጊዜ፣ የንስሃ ጊዜና እግዚአብሔርን የሚያገለግሉበት ጊዜ ተሰጥቷል።

እነሆም፣ አዳም እጁን በፍጥነት ቢዘረጋና ከህይወት ዛፍ ቢበላ፣ እርሱም እንደ እግዚአብሔር ቃልም መሠረት ለዘለአለም በኖረ፣ ለንስሃም ጊዜ ባልኖረው ነበር፣ አዎን፣ እናም ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል ባልተፈፀመና ታላቁ የደህንነት ዕቅድም በከሸፈ ነበር።

ነገር ግን እነሆ፣ ሰዎች እንዲሞቱ ተወስኗል—ስለዚህ ከህይወት ዛፍ እንደተለዩም ከምድር ገፅም እንዲሁ ይለያሉ—እናም ሰው ለዘለአለም የጠፋ ሆነ፤ አዎን የወደቀ ሆነ።

እናም እንግዲህ፣ አንተም በዚህ የመጀመሪያ ወላጆቻችን ከጌታ ፊት ለጊዜውም ይሁን በመንፈስ መለየታቸውን ትመለከታለህ፤ እናም በራሳቸው ፈቃድም ስር የነበሩ መሆናቸውንም ተመልክተሃል።

እንግዲህ እነሆ፣ ሰው ከዚህ ጊዜያዊ ሞት ደግሞ መዳኑ ትክክለኛ አልነበረም፣ ምክንያቱም ይህ ታላቁን የደስታ ዕቅድ ያጠፋዋልና።

ስለዚህ፣ ነፍስ በጭራሽ ልትሞት ስለማትችል፣ እናም የአዳም ውድቀት በሰው ዘር ላይ ሁሉ ከጌታ ፊት እንዲለዩ ጊዜያዊውን ሞት፣ እናም መንፈሳዊውን ሞት በእነርሱ ላይ በማምጣቱ፣ የሰው ዘርም ከዚህ መንፈሳዊ ሞት ደግሞ ማዳኑ አስፈላጊ ነበር።

ስለዚህ፣ እነርሱ በተፈጥሮአቸው ስጋዊ፣ ስሜታዊ፣ እናም ዲያብሎሳዊ በመሆናቸው፣ ይህ የሙከራ ጊዜ ለእነርሱ የዝግጅት ጊዜ ሆነ፤ እርሱም የመዘጋጃ ወቅት ሆነ።

፲፩ እናም አሁን ልጄ፣ ይህ የቤዛነት ዕቅድ ባይሆን ኖሮ፣ (እንዳልሆነ ቢገመት) እንደሞቱ ነፍሳቸው ከጌታ ፊት ስለምትለይ አሰቃቂ ሁኔታ ላይ እንደምትሆን አስታውስ።

፲፪ እናም እንግዲህ፣ ሰውም ባለመታዘዙ ምክንያት በራሱ ላይ ካመጣው ከወደቀበት ሁኔታ ደግሞ ለመመለስ ምንም መንገድ አልነበረም፤

፲፫ ስለዚህ፣ በፍትህ መሰረት፣ በዚህ በሙከራው ጊዜ፣ አዎን፣ በዝግጅቱ ወቅት፣ ሰዎች ንስሃ ካልገቡ በቀር የቤዛነት ዕቅድ ተግባራዊ ሊሆን አይችልም፤ በዚህ ሁኔታ ካልሆነ በቀር፣ ምህረት የፍትህን ስራ ካላጠፋው በቀር በስራ ላይ ሊውል አይችልም። እናም የፍትህ ስራ ሊጠፋ አይችልም፤ ከጠፋ ግን እግዚአብሔር አምላክ መሆኑን ያቆማል

፲፬ እናም የሰው ዘር በሙሉ የወደቁ እንደነበሩና፣ በፍትህ እጅ ላይ፣ አዎን እነርሱን ለዘለአለም ከፊቱ ለመለየት በሚመድበው የእግዚአብሔር ፍትህ ላይም እንደነበሩ እንመለከታለን።

፲፭ እናም እንግዲህ፣ የምህረት ዕቅድ የኃጢያት ክፍያው ካልተከፈለ በቀር ሊመጣ አይችልም፤ ስለዚህ፣ የምህረትን ዕቅድ ለመፈፀም፣ የፍትህን ፍላጎት ለማርካት፣ እግዚአብሔርም ደግሞ ፍፁም፣ እውነተኛ አምላክ፣ እናም መሃሪ አምላክ ይሆን ዘንድ፣ እግዚአብሔር እራሱ ለዓለም ኃጥያቶች የኃጢያት ክፍያ ይሆናልና።

፲፮ እንግዲህ፣ የተመደበ ቅጣት ከተመደበው የደስታ አላማ ጋር ተቃራኒ የሆነ፣ እንደ ነፍስ ህይወት ዘለአለማዊ የነበረው ቅጣት ከሌለ በስተቀር ለሰዎች ንሰሃ ሊመጣ አይችልም፤ የደስታ አላማም እንደ ነፍስ ህይወት ዘለዓለማዊ ነበር።

፲፯ እንግዲህ፣ ሰው ኃጢያትን ካልፈፀመ በቀር እንዴት ንስሃ መግባት ይችላል? ህግ ከሌለስ እንዴት ኃጢያትን ሊያደርግ ይችላል? ህግስ ቅጣት ከሌለ በቀር እንዴት ሊኖር ይችላል?

፲፰ እንግዲህ፣ ለሰዎች የህሊና ፀፀትን ለማምጣት የተመደበ ቅጣት፣ እናም ትክክለኛ ህግም ነበር።

፲፱ እንግዲህ፣ ህግ ባይሰጥ ኖሮ—ሰው ከገደለ መሞት ነበረበት—ከገደለ መሞትን የሚፈራ ይሆናልን?

እናም ደግሞ፣ ኃጢያትን የሚቃረን ህግም ባይሰጥ ኖሮ ሰዎች ኃጢያትን ለመፈፀም አይፈሩም ነበር።

፳፩ እናም ህግ ካልተሰጠ፣ ሰዎች ኃጢያትን ቢፈፅሙ፣ ፍትህ ወይም ምህረት ምን ማድረግ ይችሉበታል፣ በፍጥረት ላይ ምንም ጥያቄ አይኖራቸውምን?

፳፪ ነገር ግን ህጉ ተሰጥቷል፣ ቅጣቱም ተመድቧል፣ እናም ንስሃ ተፈቅዷል፤ ይህን ንስሃ መግባትን ምህረትን ትቀበላለች፤ አለበለዚያም ፍትህ ፍጡራንን ተጠያቂ ያደርጋልና ህግን ያስፈፅማል፣ እናም ህጉ ቅጣትን ያከናውናል፤ ባይሆን ኖሮ ግን የፍትህ ስራ ይጠፋ ነበር፣ እግዚአብሔርም አምላክ መሆኑን ባቆመ ነበር።

፳፫ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ መሆኑን አያቆምም፣ እናም ምህረት ንስሃ በሚገቡት ላይ ይሆናል፣ ምህረትም በኃጢያት ክፍያው አማካኝነት ይመጣል፤ የኃጢያት ክፍያም የሙታን ትንሳኤን ያመጣል፤ እናም የሙታን ትንሳኤ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር ፊት መልሶ ያመጣል፤ እንደዚህ በፍትህና በህግ መሰረት በስራቸው ሊፈረድባቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ደግመው ይመለሳሉ።

፳፬ እነሆም፣ ፍትህ የግድ ጥያቄውን ሁሉ ይጠቀማል፣ እናም ደግሞ ምህረት የራሷ የሆነውን በሙሉ የእራሷ ታደርጋለች፤ እናም በእውነት ንስሃ ከገባው በቀር ማንም አይድንም።

፳፭ ምህረት ፍትህን ይነጥቃል ብለህ ትገምታለህ? እኔ ግን እላለሁ፣ ቅንጣትም እንኳን ያህል ቢሆን አይሆንም። እንዲህ ከሆነ፣ እግዚአብሔር አምላክነቱን ያቆማል።

፳፮ እናም እግዚአብሔር ከዓለም መፈጠር ጀምሮ ያዘጋጀውን ታላቁንና ዘለአለማዊ ዓላማውን እንዲሆን እንደዚህም አድርጓል። በዚህ አይነት የሰዎች ቤዛነትና መዳን፣ እናም ደግሞ መጥፊያቸውና መከራቸው እንደዚህም መጣ።

፳፯ ስለዚህ ልጄ ሆይ፣ ማንም የሚመጣ ቢሆን ይምጣና ከህይወት ውኃ በነፃ ይካፈል፤ እና የማይመጣውም ግን እንዲመጣ አይገደድም፤ ነገር ግን በመጨረሻው ቀን እንደስራው በእራሱ ላይ በድጋሚ ይመለሳል።

፳፰ መጥፎ ማድረግን ከፈለገ፣ እናም በጊዜው ንስሃ ካልገባ፣ እነሆ፣ በእግዚአብሔር ደግሞ መመለስ መሰረት መጥፎው ነገር በእርሱ ላይ ይደረግበታል።

፳፱ እናም አሁን ልጄ፣ እነዚህ ነገሮች ከእንግዲህ እንዳያስቸግሩህ እፈልጋለሁ፤ እናም ኃጢያትህ ብቻ በዚያ ወደ ንስሃ በሚያመጣህ ጭንቀት ያስጨንቅህ።

ልጄ ሆይ፣ ከእንግዲህ ወዲያ የእግዚአብሔርን ፍትህ እንድትክድ አልፈልግም። ለራስህም የእግዚአብሔርን ፍትህ በመካድ ለእያንዳንዱ ጥልቅ ነገር በኃጢያትህ ምክንያት ለመስጠት አትጣር፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ፍትህ፣ እንዲሁም ምህረቱ፣ እናም ፅናቱ በልብህ በሙላት ተፅዕኖ እንዲያደርግ ፍቀድ፤ እናም ይህ በትህትና ወደ ምድር ያምጣህ።

፴፩ እናም እንግዲህ ልጄ ሆይ፣ ለዚህ ህዝብ ቃሉን ለመስበክ በእግዚአብሔር ተጠርተሃል። እናም አሁን ልጄ፣ መንገድህን ተጓዝ፣ ታላቁ የምህረት ዕቅድም በእነርሱ ላይ ባለቤትነት እንዲኖረው ነፍሳትን ለንስሃ ታመጣ ዘንድ፣ ቃሉን በእውነትና በጥሞና አውጅ። እናም እግዚአብሔር እንደቃሌ ይሰጥህም ዘንድ ይሁን። አሜን።