ቅዱሳት መጻህፍት
አልማ ፲፪


ምዕራፍ ፲፪

አልማ ከዚኤዝሮም ጋር ተነጋገረ—የእግዚአብሔር ሚስጥር ሊሰጥ የሚችለው ለሚታመኑበት ብቻ ነው—ሰዎች በሀሳባቸው፣ በእምነታቸው፣ በቃላቸውና በስራቸው ይፈረድባቸዋል—ኃጢአተኞች በመንፈሳዊ ሞት ይሰቃያሉ—ይህ ሞት ያለበት ህይወት የሙከራ ጊዜ ነው—የቤዛነት ዕቅድ ትንሳኤን እናም በእምነት የኃጢያትን ስርየት ያመጣል—ንስሃ የሚገቡ በአንድያ ልጅ አማካኝነት ምህረትን የመቀበል መብት አላቸው። በ፹፪ ም.ዓ. ገደማ።

አሁን አልማ የአሙሌቅ ቃል ዚኤዝሮምን ዝም ማሰኘቱን ሲመለከት፣ አሙሌቅ ዚኤዝሮም በመዋሸትና በማታለል ሊያጠፋው ሲሞክር እንደያዘው ተመልክቷልና፣ እናም ጥፋቱ በማወቁ ምክንያት መንቀጥቀጥ እንደጀመረ ስለተመለከተ፣ አፉን ከፍቶ ለእርሱ መናገርና፣ የአሙሌቅን ቃላት ማረጋግጥ፣ እናም ከዚያን በላይ የሆኑትን ነገሮች መግለጽ ወይም አሙሌቅም ካደረገው በላይ ቅዱሳት መጻሕፍትን መግለጽ ጀመረ።

አሁን አልማ ለዚኤዝሮም የተናገረው ቃላት በአካባቢው ላሉት ሰዎች ተሰምቶ ነበር፤ ህዝቡ ብዙ ነበሩና፣ እናም በዚህ መንገድ ተናገረ፤

አሁን ዚኤዝሮም በሀሰተኝነትህና በተንኮል ተይዘሀል፣ አንተ ለሰዎች ብቻ ሳይሆን ለእግዚአብሔርም ዋሽተሀልና፤ እነሆም፣ እርሱ ሀሳብህን በሙሉ ያውቃል፣ እናም ያንተ ሀሳብ በሙሉ በእርሱ መንፈስ አማካኝነት ለእኛ እንድናውቀው እንደሚሆን ትመለከታለህ፤

እንግዲህ እኛን ተሳድበህ ለመጣል ህዝቡንም ለመዋሸትና ለማታለል በእኛ ላይ ያደረከው ዕቅድህ እጅግ የረቀቀ ዕቅድ እንደሆነ እናውቃለን፣ እንደዲያብሎስም የረቀቀ ነው—

አሁን ይህ የጠላትህ ዕቅድ ነበር፣ እናም እርሱ ስልጣኑን በአንተ አሳይቷል። አሁን ለአንተ ያልኩትን ለሁሉም እንደምላቸው እንድታስታውሱ እፈልጋለሁ።

እናም እነሆ ለሁላችሁም እላችኋለሁ ይህ የጠላት ወጥመድ ነው፣ ይህም ለእርሱ እንድትገዙ ለማድረግ ለምርኮ ባለው ስልጣኑ መሰረት፣ በሰንሰለቱም ይከባችሁ ዘንድ፣ በዘለአለማዊ ጥፋት ሰንሰለት ይመታችሁም ዘንድ፣ ይህን ህዝብ ለመያዝ ያጠመደው ነው።

እንግዲህ አልማ እነዚህን ቃላት በተናገረ ጊዜ፣ ዚኤዝሮም እጅግ መንቀጥቀጥ ጀመረ፣ እርሱም በይበልጥ የእግዚአብሔርን ኃይል አምኗልና፤ እናም ደግሞ አልማና አሙሌቅ ስለእርሱ እውቀት እንዳላቸው አመነ፣ የልቡን ሀሳብና መሻት እንደሚያውቁ አምኗልና፤ በትንቢት መንፈስ መሠረት ስለእነዚህ ነገሮች እንዲያውቁ ስልጣን ተሰጥቷቸው ነበርና።

እናም ዚኤዝሮም ስለእግዚአብሔር መንግስት ይበልጥ ያውቅ ዘንድ በትጋት ይጠይቃቸው ጀመር። እናም ለአልማ እንዲህ አለው፥ አሙሌቅ ስለሙታን ትንሳኤ፣ ሁሉም ከሞት ይነሳል፣ ፃድቅም ሆነ ኃጢአተኛ፣ እናም በስራቸው እንዲፈረድባቸው በእግዚአብሔር ፊት መጥተው ይቆማሉ ያለው ምን ማለቱ ነው?

እናም አሁን አልማ እነዚህን ነገሮችን እንዲህ በማለት ማብራራት ጀመረ፣ ለብዙዎች የእግዚአብሔርን ሚስጥር እንዲያውቁ ተሰጥቷቸዋል፤ ይሁን እንጂ ለሰዎች ልጆች ለእርሱ በሚሰጡት ትኩረትና ትጋት መሰረት እንዲሰጣቸው ከሚፈቅደው የቃሉ ክፍል በስተቀር እንዳይካፈሉ ጥብቅ ትዕዛዝ ውስጥ ገብተው ነበር።

እናም ስለዚህ ልቡን የሚያጠጥር፣ እርሱም ከቃሉ ትንሹን ክፍል ይቀበላል፤ እናም ልቡንም የማያጠጥር ለእርሱ ሁሉንም በሙላት የእግዚአብሔርን ሚስጥር እስከሚያውቅ ድረስ ከቃሉ ትልቅ ክፍል ይሰጠዋል

፲፩ እናም ልባቸውን የሚያጠጥሩ ሚስጥሩን በተመለከተ ምንም እስከማያውቁ ድረስ የቃሉ ትንሽ ክፍል ይሰጣቸዋል፤ እና ከእዚያም በዲያብሎስ ምርኮ ይወሰዳሉና፣ እስከሚጠፉም በፈቃዱ ይመራሉ። እናም የሲኦል ሰንሰለትም ማለት ይህ ነው።

፲፪ እናም አሙሌቅ ሞትን በተመለከተ፣ ከሚሞት ሰውነት ወደ ማይሞት ሰውነት ስለመነሳት፣ እናም በእግዚአብሔርም የፍርድ ወንበር ፊት እንደስራችን ሊፈረድብን ስለመቅረባችን በግልፅ ተናግሯል።

፲፫ ከዚያም ልባችን ከጠጠረ፣ አዎን፣ በውስጣችን እስካማይገኝ ድረስ በቃሉ ልባችንን ካጠጠርን፣ ከዚያም በኋላ ጉዳያችን የከፋ ይሆናል፣ እንኮነናለን።

፲፬ ቃላቶቻችን ይፈርዱብናል፣ አዎን ስራዎቻችን ሁሉ ይፈርዱብናል፤ እንከን የሌለብንም በመሆን አንገኝም፣ እናም ሀሳባችንም ደግሞ ይፈርድብናል፤ እናም በዚህ አስከፊ ሁኔታ ወደ አምላካችን ለመመልከት አንደፍርም፤ እናም አለቶቹንና ተራራዎቹን ከእርሱ ፊት እንዲደብቁን በላያችን ላይ እንዲወድቁ ብናዛቸው እጅግ እንደሰታለን።

፲፭ ነገር ግን ይህ ሊሆን አይችልም፣ ወደፊቱ መምጣትና በክብሩ እናም በስልጣኑና በኃይሉ፣ በክብሩና በአለቅነቱ መቆም፣ እናም በዘለዓለማዊ እፍረታችን ፍርዱ በሙሉ ትክክል እንደሆነ፣ እርሱም በስራው ሁሉ ትክክል እንደሆነና፣ ለሰው ልጆች መሃሪ እንደሆነ፣ እንዲሁም በስሙ የሚያምኑትንና ለንስሃ የሚሆን ፍሬን የሚያስገኙትን ማንኛውንም ሰው ለማዳን ስልጣን እንዳለው እናረጋግጣለን።

፲፮ እናም አሁን እነሆ፣ እንዲህ እላችኋለሁ ሞት፣ እንዲሁም መንፈሳዊው ሞት የሆነው ሁለተኛው ሞት ይመጣል፣ ከእዚያም በኃጢአቱ ጊዜያዊ ሞትን የሚሞት መንፈሳዊ የሆነውን ሞትን ይሞትበታል፤ አዎን፣ ለፅድቅም በሆነ ነገር ሁሉ ይሞታል።

፲፯ ቅጣታቸው እንደ እሳት ባህርና ዲን፣ ነበልባሉም ከዘለዓለም እስከዘለአለም ወደ ሰማይ እንደሚወጣው የሚሆንበት ጊዜም ይህ ነው፤ እና ያም በሰይጣን ኃይልና ምርኮ መሰረት፣ እነርሱን እንደፈቃዱ ተገዢ በማድረግ፣ በዘለዓለማዊው ጥፋት የሚታሰሩበት ጊዜ ነው።

፲፰ ከዚያም፣ እላችኋለሁ፣ እነርሱም ቤዛነት እንዳልተፈፀመ ሆነው ይቆያሉ፣ በእግዚአብሔር ፍርድ መሰረት ሊድኑ አይችሉም፤ እናም መሞት አይችሉም ምክንያቱም ከእንግዲህ መበስበስ አይኖርምና።

፲፱ እንግዲህ እንዲህ ሆነ አልማ ይህንን ንግግር እንደጨረሰ፣ ህዝቡ ይበልጥ መገረም ጀመረ፤

ነገር ግን አንቲዮና የሚባል ሰው ነበር፣ በእነርሱም መካከል ዋና ገዢ የነበረው መጣና እንዲህ አለው፥ ሰው ከሞት ይነሳል እናም ከሙታን ወደማይሞተውም ይለወጣል፣ ነፍሱም በጭራሽ አይሞትም ብለህ የተናገርከው ይህ ምንድን ነው?

፳፩ የመጀመሪያ ቤተሰቦቻችን እንዳይገቡና ከህይወት ዛፍ እንዳይወስዱ እናም ለዘለአለም እንዳይኖሩ እግዚአብሔር ኪሩቤልንና የነበልባሉን ሰይፍ በዔድን ገነት በስተምስራቅ አስቀምጧል በማለት ቅዱሳን መፃህፍትስ የተናገሩት ምን ማለት ነው? እናም ለዘለአለም እንዲኖሩ ምንም እድል እንዳልነበረ እንመለከታለን።

፳፪ አሁን አልማ እንዲህ አለው፥ እኔ እንድገልፀው የነበረው ነገር ይህ ነው። አሁን አዳም በእግዚአብሔር ቃል መሰረት የተከለከለውን ፍሬ በመመገቡ መውደቁን ተመልክተናል፤ እናም በመውደቁ የሰው ዘር በሙሉ የሚጠፋና የሚወድቅ እንደሆነም በዚህ እናያለን።

፳፫ እናም አሁን እነሆ እላችኋለሁ፣ በዚያን ጊዜ ለአዳም ከህይወት ዛፍ ፍሬ መመገብ የሚቻለው ቢሆን ኖሮ፣ ሞት አይኖርም ነበር፣ እናም ቃሉም ዋጋ የሌለው ይሆን ነበር፣ ይህንን በበላችሁ ጊዜ በእርግጥ ትሞታላችሁ ብሎም ተናግሮ ነበርና፣ እግዚአብሔርንም ውሸታም ያደርገው ነበር።

፳፬ እናም ሞት፣ አዎን፣ በአሙሌቅ የተነገረው ጊዜያዊ ሞት በሰው ዘር ላይ መምጣቱን እንመለከታለን፤ ይሁን እንጂ የሰው ልጅ ንስሃ ይገባ ዘንድ የተሰጠው ጊዜ ነበር፣ ስለሆነም ይህ ህይወት የሙከራ ጊዜ፣ እግዚአብሔርን ለመገናኘት የመዘጋጃ ጊዜ፣ ከትንሣኤ በኋላ ለሚሆነው እኛ ለተነገርነው መጨረሻ ለሌለው ሁኔታ መዘጋጃ ጊዜ ይሆናል።

፳፭ አሁን፣ ከዓለም መፈጠር ጀምሮ በነበረው የቤዛነት ዕቅድ ባይሆን ኖሮ፣ የሙታን ትንሳኤ ሊሆን ባልቻለም ነበር፣ ነገር ግን የተነገረውን የሙታን ትንሳኤ የሚያመጣ የቤዛነት ዕቅድም ተዘጋጅቶ ነበር።

፳፮ እናም አሁን እነሆ፣ የመጀመሪያ ወላጆቻችን ሄደውና የህይወት ዛፍን መመገብ ቢችሉ ኖሮ የሚዘጋጁበት ሁኔታ ሳይኖራቸው ለዘለዓለም ደስታ የሌላቸው በሆኑ ነበር፤ እናም የቤዛነት ዕቅድም በከሸፈና የእግዚአብሔር ቃል ውጤት ሳይኖረው ዋጋ የሌለው በሆነም ነበር።

፳፯ ነገር ግን እነሆ፣ እንዲህ አልነበረም፤ ነገር ግን ሰዎች መሞት እንዳለባቸው ተመድቦ ነበር፣ እናም ከሞት በኋላ፣ ለፍርድ፣ እንዲሁም እኛ የተናገርነው ዓይነት የመጨረሻ ለሆነ ፍርድ መምጣት አለባቸው።

፳፰ እናም እግዚአብሔር እነዚህ ነገሮች ለሰው ልጆች መምጣት እንዳለባቸው ከመደበ በኋላ፣ እነሆ፣ ሰዎችም የተወሰነላቸውን ነገር በተመለከተ ማወቅ እንደነበረባቸው ተመለከተ፤

፳፱ ስለዚህ ከእነርሱ ጋር እንዲነጋገሩ፣ ሰዎችንም ክብሩን እንዲመለከቱ ያደረገ መላዕክት ላከ።

እናም ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስሙን መጥራት ጀመሩ፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ተነጋገረ፤ እናም ከዓለም መፈጠር ጀምሮ ተዘጋጅቶ የነበረውን የቤዛነት ዕቅድም እንዲያውቁ አደረገ፣ እናም ይህን እንዲያውቁ ያደረገው በእምነታቸውና በንስሃቸው እንዲሁም በቅዱሱ ስራቸው መሰረት ነው።

፴፩ ስለዚህ፣ ጊዜያዊ የነበሩትንም ነገሮች በተመለከተ የመጀመሪያዎቹን ትዕዛዛት በመተላለፋቸው፣ እናም እንደ አማልክት መልካሙን ከክፉ እንዲያውቁ በመሆናቸው፣ እራሳቸውን ለመስራት በሚችሉበት ሁኔታ፣ ወይም እንደፍላጎታቸውና እንደደስታቸው፣ ክፉ ወይንም መጥፎውን ለማድረግ በሚችሉበት ቦታ እያሉ፣ ለሰዎች ትዕዛዛትን ሰጠ፣

፴፪ ስለዚህ እግዚአብሔር ስለቤዛነት ዕቅድ እንዲያውቁ ካደረገ በኋላ፣ ቅጣቱ ሁለተኛ ሞት፣ ይህም ጻድቃንን በሚመለከት ነገሮች የዘለአለም ሞት በሆነው መጥፎ እንዳይሰሩ ትዕዛዛትን ሰጣቸው፤ ለእንደነዚህ ዓይነቱ የቤዛነት ዕቅድ ኃይል ሊኖረው አይችልምና፣ ምክንያቱም በቸሩ አምላክ ኃያልነት የፍርድ ስራዎች ሊጠፉ አይቻላቸውምና።

፴፫ ነገር ግን እግዚአብሔር በልጁ ስም ሰዎችን ጠራ፣ (ይህም የተዘረጋው የቤዛነት ዕቅድ ነው) እንዲህም አለ፥ ንስሃ የምትገቡ፣ እናም ልባችሁን የማታጠጥሩ ከሆነ፣ ከዚያም በአንድያ ልጄ አማካኝነት ምህረትን አደርግላችኋለሁ።

፴፬ ስለዚህ፣ ማንኛውም ንስሃ የሚገቡ እናም ልባቸውን የማያጠጥሩ ለኃጢአታቸው ስርየት በአንድያ ልጄ አማካኝነት ምህረት ይገባቸዋል፤ እና እነዚህም በእረፍቴ ይገባሉ።

፴፭ እናም ማንኛውም ልባቸውን የሚያጠጥሩና ክፋትን የሚያደርጉ፣ እነሆ፣ በእረፍቴ እንደማይገቡ በቁጣዬ እምላለሁ።

፴፮ እናም አሁን፣ ወንድሞቼ፣ እነሆ እንዲህ እላችኋለሁ፣ ልባችሁን የምታጠጥሩ ከሆነ በጌታ እረፍት ውስጥ አትገቡም፤ ስለዚህ መተላለፋችሁ ቁጣውን በእናንተ ላይ በመጀመሪያ ጥፋት እንዳደረገው እንዲልክ ያነሳሳዋል፣ አዎን፣ ለዘለዓለም ለነፍሳችሁ ጥፋት እንደቃሉ የመጨረሻ ቁጣውን እንደ መጀመሪያው ይልካል፣ ስለዚህ በቃሉ መሰረት በመጀመሪያው ሞት ልክ እንደ መጨረሻው ይሆንባችኋል።

፴፯ እናም አሁን፣ ወንድሞቼ፣ እነዚህን ነገሮች ስለምናውቅና፣ እውነት በመሆናቸው፣ ንስሃ እንግባና ልባችንን አናጠጥር፣ እግዚአብሔር ለእኛ በሰጠው በሁለተኛው ትዕዛዝ ቁጣውን በእኛ እንዲያደርግም አንቀስቅሰው፤ ነገር ግን በቃሉ መሰረት ወደተዘጋጀው የእግዚአብሔር እረፍት እንግባ።